Print this page
Sunday, 13 May 2018 00:00

የ104 አመቱ ዝነኛ ሳይንቲስት በፈቃዳቸው ተገደሉ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 “ደስ የሚል ህይወትን ኖሪያለሁ፤ አሁን ግን መኖር በቃኝ፤ የመሞት መብቴን አክብሩልኝና በክብር አስናብቱኝ” ያሉት ታዋቂው አውስትራሊያዊ ሳይንቲስት ዴቪድ ጉዶል፤ የመሞት መብታቸው ተከብሮላቸው በተወለዱ በ104 አመት ዕድሜያቸው ከትናንት በስቲያ፣ ስዊዘርላንድ ውስጥ በሚገኝ ክሊኒክ ተገድለዋል፡፡
12 የልጅ ልጆችን ያዩት ሳይንቲስቱ፤ ራሳቸውን ለሞት ሲያዘጋጁ በነበሩበት ዋዜማ ምናልባት ሃሳባቸውን ይቀይሩ እንደሆን የመጨረሻ ቃላቸውን እንዲሰጡ ተጠይቀው፣ በህይወት መቀጠል አልፈልግም፣ ልክ ነገ ላይ ህይወት እንድታበቃ የማድረግ እድል ስላገኘሁ ደስተኛ ነኝ ሲሉ ምላሽ መስጠታቸውን ዩኤስኤ ቱዴይ ዘግቧል፡፡
ሳይንቲስቱ የስዊዘርላንድ ህግ በሚፈቅደው መሰረት ሶዲየም ፔንቶባርቢታል የተባለ አደገኛ መድሃኒት የተሞላበት ስሪንጅ በሃኪሞች ከተሰጣቸው በኋላ፣ መርፌውን ራሳቸው ክንዳቸው ላይ እንዲወጉት ተደርጎ፣ በደቂቃዎች ውስጥ የመጨረሻው እንቅልፍ እንደወሰዳቸውና ከቅጽበት በኋላም ይወስዳቸው ዘንድ የፈቀዱለት ሞት እሹሩሩ እያለ ወደማይመለሱበት እንደወሰዳቸው ዘገባው ጠቁሟል፡፡
የመሞት መብት እንዲከበር የሚታገል አለማቀፍ ተሟጋች ተቋም አባል የነበሩት የ104 አመቱ የዕድሜ ባለጸጋ ዴቪድ ጉዶል፤ ምንም እንኳን ከቅርብ አመታት ወዲህ ከዕድሜ መግፋት ጋር በተያያዘ የጤና ችግር ቢያጋጥማቸውም ለሞት የሚያሰጋ እንዳልነበርና ለመሞት የወሰኑት ህይወት በቃችኝ በሚል ብቻ መሆኑንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
በእንግሊዝ፣ በአሜሪካና በአውስትራሊያ በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት ለረጅም አመታት ያገለገሉትና በሙያቸው ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ የአውስትራሊያን የክብር ሜዳልያ የተሸለሙት ሳይንቲስቱ፤ እ.ኤ.አ በ1979 ጡረታ መውጣታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ 30 ቅጾች ያሉትንና ከ500 በላይ ታዋቂ ሳይንቲስቶች የጻፏቸው የምርምር ስራዎች የተካተቱበትን ኢኮስስተምስ ኦፍ ዘ ወርልድ የተባለ መጽሃፍ በአርታኢነት ለንባብ ማብቃታቸውንም አመልክቷል፡፡
በፈቃዳቸው ይህቺን አለም የተሰናበቱት ዴቪድ ጉዶል፤ ሬሳቸው እንዳይቀበር፤ ሰልስትና አርባ ብሎ ነገር እንዳይደረግላቸው የተናዘዙ ሲሆን የሰውነት ክፍሎቻቸው ለሌሎች ሰዎች ህክምና እንዲሰጥላቸውና አስከሬናቸው እንዲቃጠልም ለቤተሰቦቻቸው አደራ ብለው እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 2451 times
Administrator

Latest from Administrator