Print this page
Saturday, 12 May 2018 11:17

ለ9ኛ ጊዜ የኢቦላ ወረርሽኝ በተከሰተባት ኮንጎ 17 ሰዎች ሞተዋል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

    በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሰሜን ምዕራብ ክልል የኢቦላ ቫይረስ ዳግም በወረርሽኝ መልክ መቀስቀሱንና በአካባቢው ለህልፈተ ህይወት ከተዳረጉ 17 ሰዎች መካከል ሁለቱ በቫይረሱ ሳቢያ መሞታቸው መረጋገጡን የአገሪቱ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ቢኮሮ ከተባለቺው የአገሪቱ ከተማ አቅራቢያ በምትገኘው ኢኮ ኢምፔንጄ የተሰኘች የገጠር መንደር ውስጥ የሚኖሩ 21 ሰዎች ባለፈው ሳምንት መታመማቸውንና ከእነሱ መካከልም 17ቱ ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ የተቀሩት በሆስፒታል ውስጥ ክትትል እየተደረገላቸው እንደሚገኙ ገልጧል፡፡
ስምንት ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ በቁጥጥር ስር ከዋለ አንድ አመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በአገሪቱ ታሪክ ዘጠነኛው የሆነው የኢቦላ ወረርሺኝ  ከሰሞኑ መከሰቱን የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ አፋጣኝ ርብርብ ካልተደረገ ወረርሽኙ የከፋ ጥፋት ሊያስከትል ይችላል መባሉን አመልክቷል፡፡
የአገሪቱ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ወረርሺኙን በአፋጣኝ ለመግታትና ለዜጎች አፋጣኝ ህክምና ለመስጠት ባለሙያዎችን መድቦ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝ በመጠቆም፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ ችግሩን ለመፍታት ርብርብ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
የአለም የጤና ድርጅት በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የተቀሰቀሰውን የኢቦላ ወረርሺኝ ለመግታት በአፋጣኝ ልዩ ግብረሃይል በማቋቋምና 50 ባለሙያዎችን በማሰማራት ከአገሪቱ መንግስትና ከለጋሽ ተቋማት ጋር በጥምረት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጾ፣ አለማቀፉ ማህበረሰብ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግም ጥሪ አቅርቧል፡፡
ከሁለት አመታት በፊት በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰውና በታሪክ የከፋው እንደነበር የሚነገርለት የኢቦላ ወረርሺኝ፤ በአካባቢው አገራት በድምሩ 11 ሺህ 300 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት መዳረጉንና 28 ሺህ 600 ያህል ሰዎችም በቫይረሱ መጠቃታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 1355 times
Administrator

Latest from Administrator