Saturday, 28 April 2012 14:42

ማን ዩናይትድ በዋጋው፤ የእንግሊዝ

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(2 votes)

ክለቦች በማሊያቸው ገበያውን ይመራሉ

=ማንችስተር ሲቲ በሜዳው ኢትሃድ ስታድዬም ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች 17ቱን አሸንፏል፡፡

በውድድር ዘመኑ ለ1 ዋንጫ ብቻ ያነጣጠረው ማንችስተር ዩናይትድ ባለፈው 1 ዓመት የዋጋ ተመኑን 20 በመቶ በማሳደግ 2.2 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ ክለብ መሆኑ ተገመተ፡፡ የአውሮፓ ክለቦችን የገቢ መጠን፤ ትርፋማነትና የእዳ እና ብድር ደረጃ በማስላት በፎርብስ መፅሄት ጥናት ይፋ የተደረገው ሪፖርት እንዳመለከተው ማን ዩናይትድ በዋጋ ግምት የመጀመርያው ክለብ ሲሆን ዘንድሮ ለተከታታይ 8ኛ ዓመት ነው፡፡ ከአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግና ከፕሪሚዬር ሊግ ውድድሮች ከሩብ ፍፃሜ የተሰናበተው ክለቡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ 20ኛውን የሻምፒዮናነት በማስመዝገብ አዲስ ታሪክ ለመስራት እየገሰገሰ ነው፡፡ ማን ዩናይትድ ከሜዳ ውጭ በሲንጋፖር የአክሲዮን ገበያ ጥሩ እየሸቀለ መሆኑም ይገለፃል፡፡ በፎርብስ መፅሄት ሪፖርት መሰረት የስፔኖቹ ክለቦች ሪያል ማድሪድ እና ባርሴሎና በ1.88 ቢሊዮን ዶላርና በ1.3 ቢሊዮን ዶላር ዋጋቸው ማን ዩናይትድን ይከተላሉ፡፡ ባለፈው 1ዓመት ባርሴሎና በ34 በመቶ ሪያል ማድሪድ በ29 በመቶ የዋጋ ግምታቸው ማደግ ችሏል፡፡

አምና የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ በአጠቃላይ ከውድድሩ ገበያ ያገኘውን 1.14 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ለተሳታፊዎቹ 32 ክለቦች ማዳረሱ ለአውሮፓ እግር ኳስ የገቢ እድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ በተለይ ከብሮድካስት መብት ገቢ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እሰከ 1.28 ቢሊዮን ዶላር ማስገኘቱ የክለቦች ገቢ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል፡፡

በዓለም ዙርያ 330 ሚሊዮን ደጋፊዎች ማሰባሰበ የሚገለፀው ማን ዩናይትድ በዋጋ ግምቱ ለማደጉ ዋና ምክንያት ሆኖ የተጠቀሰው ባንድ የውድድር ዘመን በብሮድካስት መብቱ በሚያገኘው እስከ 192 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ዓመታዊ ገቢው ነው፡፡ ባርሴሎና ግን በየዓመቱ ከተመሳሳይ የገቢ ምንጭ 266 ሚሊዮን ዶላር በማካበት ከየትኛው ክለብ የላቀ ድርሻ ይዟል፡፡ ሪያል ማድሪድ በየዓመቱ 214 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማንቀሳቀስ ከማን ዩናይትድ የበለጠ ሲሆን ከኣዲዳስ፤ ከኤምሬትስ ኤርላይንስና ከቢዊን ጋር በገባው ውል በባየር ሙኒክ ብቻ የተበለጠ 250 ሚሊዮን ዶላር አግኝቷል፡፡ባየር ሙኒክ በተለያዩ የንግድ ገቢዎቹ 258 ሚሊዮን ዶላር በማስገባት ቀዳሚ ሆኗል፡፡ በፎርብስ  መፅሄት የገቢ ትንተና መሰረት በዓመታዊ ገቢው 532 ሚሊዮን ዶላር የሚያንቀሳቅስው ማን ዩናይትድ ከዋጋ ግምቱ 32 በመቶ እዳ አለበት፡፡  ሪያል ማድሪድ 214 ሚሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ  እያንቀሳቀሰ ከዋጋ ግምቱ 13 በመቶውን በእዳ አስየዞ ባርሴሎና በ695 ሚሊዮነ ዶላረ ዓመታዊ ገቢና ከዋጋ ተመኑ 54 በመቶን እዳ በማስመዝገብ ተጠቅሰዋል፡፡  እንደ ፎርብስ መፅሄት ከሆነ ከቢሊዮን ዶላር በላይ ዋጋቸው በመተመን 5 ክለቦች ሲሆኑ በቀሪዎቹ  ደረጃዎች አርሰናል 1.292 ሚሊዮን ዶላ የዋጋ ተመኑ 4ኛ ባየር ሙኒክ  1.24 ቢሊዮን ዶላር ግምት አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ ኤሲ ሚላን በ761 ሚሊዮን ዶላር ስድስተኛ ደረጃ ሲይዝ የአብራሞቪቹ ቼልሲ ደግሞ በ619 ሚሊዮን ዶላር 7ኛ ነው፡፡

የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቦች በማልያቸው ዋጋም አውሮፓን ይመራሉ፡፡ በሊጉ የሚወዳደሩ 20 ክለቦች ከማልያ ጋርበተያያዘ ባላቸው የገቢ ውሎች በድምሩ 90 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ አላቸው፡፡ የሚገርመው ከ5ቱ የአውሮፓ ታላቅ ሊጎች የእንግሊዝ ክለቦች ማልያዎች ዋጋ ርካሽ መሆኑ ነው፡፡ የዘንድሮ የአውሮፓ እግር ኳስ የትጥቅ አቅራቢ ሪፖርት ሰሞኑን ይፋ ያደረገው ስፖርት ተ ማርከት የተባለ ተቋም ነው፡፡ በሪፖርቱ መሰረት የእንግሊዝ ክለቦች ለስፖርት ትጥቅ አምራችና አቅራቢ ኩባንያዎች የገበያ ሁኔታ ማራኪ አቅም በመያዛቸው እያንዳንዱ ክለብ በየዓመቱ እስከ 4.5 ሚሊዮን ፓውንድ በአማካይ  እያገኘ ነው፡፡ በሌሎች የአውሮፓ ሊጎች የክለብ አማካይ የትጥቅ ገቢ 2.7 ሚሊዮን ፓውንድ እንደሚተመንም ተመልክቷል፡፡ ዘንድሮ ፕሪሚዬር ሊጉ 4 ሚሊዮን የክለብ ማልያዎች ያሸጠ ሲሆን በዓለም እግር ኳስ በስታድዬም ገቢዎች ብዛት የሚታወቀው ቦንደስ ሊጋ ከሚሸጠው የክለቦች ማልያ በእጥፍ ብልጫ ይኖረዋል፡፡ በስፖርት ተ ማርክት እንደተገለፀው ከማልያና ከተለያዩ ምርቶች በአውሮፓ ታላግ ሊጎች ያሉ ክለቦች አጠቃላይ ገቢ ባለፈው 5 ዓመት በ48 በመቶ እድገት አሳይቷል፡፡ በአምስቱ ታላቅ ሊጎች የትጥቅ አቅራቢነት ትልልቆቹ አዲዳስና ናይክ በሰፊው ቢቆጣጠሩትም ከ27 በላይ ኩባያዎች እየሰሩ ናቸው፡፡ ለእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ ለስፔን ፕሪሚዬር ሊጋ፤ ለጣሊያን ሴሪኤ ፤ ለጀርመን ቦንደስ ሊጋና ለፈረንሳይ ሊግ 1 ክለቦች ሁለቱ ትጥቅና የስፖርት እቃ አቅራቢና አምራች ኩባንያዎች አዲዳስና ናይክ 44 በመቶ ድርሻ በመያዝ 270 ሚሊዮን ፓውንድ ኢንቨስት አድርገዋል፡፡ በስፖርት ማርክት በተሰራው ጥናት የእንግሊዝ ክለቦች ማልያ 40 ፓውንድ ሲያወጣ የላሊጋውና የሴሪኤ ክለቦች ማልያዎች እስከ 60 ፓውንድ እየተቸበቸቡ ናቸው፡፡

 

 

 

Read 6123 times Last modified on Saturday, 28 April 2012 14:46