Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 28 April 2012 14:35

“ማንም ሳይታከም እንዲመለስ አልፈልግም”

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በ13ሚ. ብር የተከፈተ ሆስፒታል አገልግሎት መስጠት ጀምሯል

አብዛኞቹ ሃብታሞች ስኳርና ደም ግፊት ከጣላቸው በኋላ ይመጣሉ

በእግር መሄድና መስራት ጤነኛነትን አያረጋግጥም

“ማንም ሳይታከም እንዲመለስ አልፈልግም”

በውጭ አገራት የመስራት ዕድሉ እያለዎት እንዴት ወደ አገርዎ ተመለሱ?

ብዙ አገሮች ለመሄድም ሆነ ለመስራት እድሉ ነበረኝ፡፡ ከአረብ አገራት እስከ አውሮፓና አሜሪካም ሔጄም አይቼዋለሁ፡፡ ሆኖም ኢትዮጵያ ውስጥ ሠርቼ ለውጥ አመጣለሁ ብዬ ስላሰብኩ ወደ ሌላ አገር መሄድ አልፈለግሁም፡፡ ሁሌም የምመኘውና የማስበው አገርና ወገንን ማገልገል ብቻ ነው፡፡ ለዚህም ነው በ1997 ዓ.ም ወደ አገሬ ተመልሼ የመጣሁት፡፡ እንደመጣሁ ዘንባባ ሆስፒታል ተቀጠርኩ፡፡ በትርፍ ሰአቴ አፍሪካ ክሊኒክ እና ፖሊስ ሆስፒታል እሠራ ነበር፡፡ ፖሊስ ሆስፒታል አሁንም እየሰራሁ ነው፡፡

 

ግብጽ አገር በአብዛኛው የሚከሰቱ የተለዩ የበሽታ አይነቶች አሉ…

ግብጽ ጉበት፣ ስኳር፣ ደም ግፊት ይበዛል፡፡ እዚህ ኢንፌክሽን የሆኑ ነገሮች ይበዛሉ፡፡ ወባ ቲቢ፣ ኤችአይቪ የመሳሰሉት ይበዛሉ፡፡ እኔ ደግሞ እዚህ ኢንፌክሽንን በተመለከተ ትምህርት ስለወሰድኩ ለግብፆች ሞዴል ነበርኩ፡፡ እዚህ ስመጣ ደግሞ አለርጂንና  በተፈጥሮ የሚመጡ የውስጥ ደዌን በተመለከተ ስፔሻላይዝድ ስላደረግሁ ሞዴል እሆናለሁ ማለት ነው፡፡ ስፔሻሊስት ሆኛለሁ፡፡ በውስጥ ደዌ ህክምና ብዙዎች በአንድ ነገር ላይ ብቻ ነው እስፔሻላይዝ የሚያደርጉት፡፡ እኔ ግን ከአፍ ጀምሮ እስከ ሠገራ መውጫ ድረስ ጨጓራ፣ ጉበት፣ አንጀት፣ ጣፊያ፣ ትንሿ አንጀትን በተመለከተ ስፔሻላይዝ አድርጌአለሁ፡፡

የትኛው የውስጥ ክፍላችን ቶሎ ለበሽታ ይጠቃል?

ሳንባ በውስጥ ደዌ ይጠቃለላል፡፡ ልብ እንደዚሁ ስፔሻላይዝ ሲደረግ ነው ሁሉንም ማወቅ የሚቻለው፡፡ እስካሁን ወደዚህ ሆስፒታል የመጡት የጨጓራ፣ የጉበት፣ የሳንባና የውስጥ ችግር ያለባቸው ናቸው፡፡ የጉበት የጨጓራና የአንጀት ታካሚዎች ባብዛኛው ይመጣሉ ማለት ነው፡፡

እነዚህ ህመሞች ከምንድነው የሚከሰቱት?

ጉበት ማለት በሰውነታችን የሚገኝ ትልቅ ኦርጋን ነው!! የአንድ ሰው ጉበት እስከ 1.5 ኪሎ ግራም ሊመዝን ይችላል፡፡ “ሜታ ቦዲ” የሚባሉ የሰውነት ክፍሎችን በሙሉ የሚቆጣጠር ነው፡፡ በሰውነታችን ያሉትን ስቦችን የሚያከማችና የሚሠራም ሲሆን የበሽታ መከላከያን ያመርታል፡፡ ይሄ ጉበት በተለያየ ነገር ሊጠቃ ይችላል፡፡ ዋነኛው ቫይረስ ኢንፌክሽን የሚባለው ሲሆን ከA-G ያሉ የጉበት ቫይረስ በሽታዎች አሉ፡፡ ባክቴሪያ ፕሮቶዝዋ የሚባሉም አሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የኬሚካሎች ችግር አለ፡፡ የማደንዘዣ መድሃኒቶች፣ የቲቢ መድሀኒቶችና የኤችአይቪ መድሀኒቶች ጉበትን ሊነኩ የሚችሉ ይችላሉ፡፡ አልኮልም ጉበትን ሊያጠቃው ይችላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተፈጥሮ ኢንዛይሞች የጐደሉት ጉበት ሊኖር ይችላል፡፡ የባህል መድሃኒቶች መጠናቸው እና ምንነታቸው ያልታወቁ በመሆናቸው ጉበትን ሊጐዱ ይችላሉ፡፡ ካንሰር ሊያመጣም ይችላል የሀሞት ጠጠር መንገድ ሲዘጋበት የሀሞት አሲዱ ወደ ኋላ ተመልሶ ጉበትን ሊያጠቃ ይችላል፡፡

መፍትሔው ምንድነው?

ኤቢ ታይተስ ቢ ቫይረስ ክትባት መውሰድ መፍትሔ ነው፡፡ በአገራችን 10% ኤቢታይተስ ቢ ጉበት አለ፡፡ ከ19 አመት በታች የሆኑ ሰዎች ለጉበት በሽታ ይጋለጣሉ ተብሎ ስለሚታሰብ መመርመር ያለባቸው ሲሆን ባልና ሚስት ከሆኑ አንዱ ቢኖርበት ሌላኛው ክትባቱን መውሰድ ይችላል፡፡ ሀኪሞችና የጤና ባለሙያዎች በሙሉ ክትባቱን ማግኘት አለባቸው፡፡ አልኮል የሚወስዱ ለጉበት ተጋላጭ ይሆናሉ፡፡ መድሃኒቶችን ዝም ብለው የሚወስዱና ምንነታቸው ያልታወቁ መድሀኒቶችን የሚወስዱ ሰዎች መጠንቀቅ አለባቸው፡፡

የጨጓራ ህመም ምክንያቱ ምንድነው?

የጨጓራ ሥራ ምግብን ማድቀቅ እና ምግብ ሁሉ ተጣርቶ ወደ ሰውነታችን እንዲገባ ማድረግ ነው፡፡ ጨጓራ እራሱን እንዲከለክል ባይካርቦኔት፤ የመሳሰሉ ነገሮችን ያመነጫል፡፡ አንዳንድ ሰዎች በተፈጥሮ ብዙ “ሃይፐር አሲድ” ይረጫሉ፡፡ ትንሽ አሲድ ተረጭቶ ለአሲድ ተጋላጭ የሚሆኑ አሉ፡፡

እንዲያ ሲሆን በኢንዶስኮፒ በመታየት ደሙ ተመርምሮ ህክምና ማግኘት አለበት፡፡ ሰውነታቸው ሴንሲቲቭ ስለሆነ ቶሎ ህክምና ያስፈልጋቸዋል፡፡ ዋናው ነገር ጨጓራችን እራሱ አሲድ ይረጫል፡፡ ለምግብ ዳይጄሽን ነው የሚረጨው፡፡ ስለዚህ ምግባችንን በሰአቱ መውሰድና ብዙ ውሃ መጠጣት፣ ከእጅ ወደ አፍ የሚገባ ባክቴሪያ ስላለ ከዚያ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ በተረፈ ንጽህናችንን መጠበቅ፤ የጨጓራ ህክምና መውሰድ መፍትሔ ነው፡፡

ሆስፒታሉ ስራ ከጀመረ ምን ያህል ጊዜ ሆነው?

ሆስፒታላችን አሚን ጠቅላላ ሆስፒታል ይባላል፡፡ ጠቅላላ ህክምናና የህፃናት ህክምና፣ እንዲሁም የማወለጃ አገልግሎት እንሠጣለን፡፡ አሚን ማለት ይሁን ማለት ነው፡፡ ስያሜው የልጄን ስም የያዘ ነው፡፡ ስራ ከጀመረ ሁለት ሳምንት ሆኖታል፡፡ እስካሁን አምስት መቶ ታካሚዎች ታክመዋል፡፡ እኔ ማንም ሰው በገንዘብ እጦት እንዲመለስ አልፈልግም፡፡ በድንገተኛ የሚመጡ ታካሚዎች ቅድሚያ አገልግሎቱን እንዲያገኙ ነው የምናደርገው፡፡ ሁሉም በህክምናው እረክተው እንዲሄዱ እፈልጋለሁ፡፡ ሆስፒታሉ 40 የህክምና ባለሙያዎች ሲኖሩት ስምንት ያህሉ ስፔሻሊስቶች ናቸው፡፡

ወጪው ምን ያህል ነው?

ህንፃውን ለማደስ እና ለተለያዩ የህክምና መሳሪያዎች 13 ሚሊዮን ብር አውጥቻለሁ፡፡ በወር ለህንፃው 100ሺህ ብር እከፍላለሁ፡፡ ይሄንን ያደረግሁት የህብረሰቡን ጤንነት በመጠበቅ አገሬንና ወገኔን ለማገልገል በማሰብ ነው፡፡

ሰዎች ጤንነታቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ ምን ይላሉ?

ሰዎች ለጤናቸው ትኩረት መስጠት አለባቸው፡፡ ወጥተን ለመግባትና የፈለግነውን ለማድረግ ጤና ወሳኝ ነው፡፡ ብዙዎቹን ህመሞች በቀላሉ ማዳን ሲቻል ሲወድቁ የሚመጡ ሰዎች አሉ፡፡ ከገቢያችን አንዷን ብር ለህክምና ብለን ብናስቀምጥ አንጐዳም፡፡ አለመታመም ወይም ቆመን መሄድ አሊያም ሥራ መስራት ጤነኛነትን አያረጋግጥም፡፡  ሰውነታችን ባለው አቅም ከተቋቋመ በኋላ  መጨረሻ ላይ ሲሸነፍ ነው የምንታመመው፡፡ በራሳችን ንጽህና ጉድለት ቀላል የሆኑ ገዳይ በሽታዎችን ልናመጣ እንችላለን፡፡ ምግቦቻችንን በንፅህናና በደንብ አብስለን በሰአቱ መመገብ ይገባናል፡፡ አብዛኛዎቹ ሀብታሞች ስኳርና ደም ግፊት ከጣላቸው በኋላ ይመጣሉ፡፡ አንድም ቀን ስኳርና ደማቸውን አላስለኩም፡፡ ስኳር አንዴ አይደለም የሚታየው በቆይታ ሊሆን ይችላል፡፡ የሴቶች የማህፀን ግድግዳዎች ለካንሰር ይጋለጣል፤ ቶሎ ቢታወቅ ግን ይድናል፡፡ እንደዚህ አይነት በርካታ ችግሮች ሊመጡ ስለሚችሉ ህብረተሰቡ ጤናውን መጠበቅ ያለበት ከመውደቁ በፊት ነው፡፡

 

 

Read 5667 times Last modified on Saturday, 28 April 2012 14:40