Tuesday, 20 March 2018 11:37

“ህልሜ በሥራዎቼ ጠንካራ ንቅናቄ መፍጠር ነው”

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 “--አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለዓይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም፡፡--”

    ተወልዶ ያደገው በጎጃም ገጠር ቢሆንም ያደገውና የተማረው በባህርዳር ከተማ ነው - ሰዓሊ እያዩ ገነት፡፡ የመጀመሪያ ድግሪውን ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ ቢያገኝም የነፍሴ ጥሪ እንዳልሆነ ስገነዘብ፣የወርልድ ቪዥን ሥራዬን ጥዬ፣ ወደ አዲስ አበባ መጣሁና የስዕል ት/ቤት ገባሁ ይላል፡፡ በትምህርቴ “ሰቅዬ” በመቅረት በስዕል    ት/ቤት ውስጥ የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል እምነት ነበረኝ የሚለው ሰዓሊው፤ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ ብሏል፡፡ በፋይን አርት ዲግሪውን ከአገኘ በኋላስ? የጥበብ ጉዞው ምን ይመስላል? ወደ ባህርዳር ይዤው ሄድኩ ስለሚለው ህልሙ ያወጋናል፡፡ ስዕል እንጀራ አይሆንም በሚል የሚንጸባረቀውን  አመለካከትም ይሞግታል። ስለ ምዕራቡ ዓለም የሥነ ጥበብ ፍልስፍና፣ “ነቁጥ” በሚል ስያሜ በጉራማይሌ የሥነጥበብ ጋለሪ ለዕይታ ስላቀረበው አውደ ርዕይ ያብራራል፡፡ ሰዓሊው በቅርቡ በግብጽና በኢኳዶር በሚካሄድ የሥነ ጥበብ ሲምፖዚየም ላይ እንደሚሳተፍም ይገልጻል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ሰዓሊውን በጥበብ ህይወቱ ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡ እነሆ፡-  


   ስሜትህ ለስነ-ጥበብ እያደላ እንዴት ኢኮኖሚክስ ለመማር ዩኒቨርሲቲ ገባህ?
“ብልጥ ልጅ እየበላ ያለቅሳል” ይላሉ አበው። በውስጤ የስነ-ጥበብ ፍቅር ቢኖረኝም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተገብቶ መማር እንደሚቻል የነገረኝ ወይም መንገዱን ያሳየኝ አልነበረም፡፡ ብቻ ባህርዳር ላይ ዘውዱ ባይሌ የሚባል ሰዓሊ ነበር (ነፍሱን ይማርና) ጋለሪ ከፍቶ የማስታወቂያ ስራ ሲሰራ እያየሁ፣ እሱን ነበር መሆን የምፈልገው፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የትምህርት ውጤቴ ጥሩ ስለነበር ካሉት ትምህርቶች የተሻለ ነው ብዬ ያመንኩትን የኢኮኖሚክስ ትምህርት ልማር ቻልኩኝ፡፡
በተማርከው ትምህርት ሰራህበት ታዲያ? ከዚያስ እንዴት ወደ አለ የስነ ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ገባህ?
በኋላ ላይ ጥሪሽ እንዳልሆነ ሲገባሽ ሁሉም ነገር ትግልና ፈተና ይሆንብሻል፡፡ ላልተፈጠርንበት አላማ ምናልባት ችለን በእጃችን ልንሄድ እንችላለን ግን እጅ እንደ እግር እንደማይሆን የተረዳን ሰዓት፣ በእግር መሄድ ስንሞክርና በጣም ምቹ መሆኑን ስንረዳ በእጃችን የሄድንበትን ጊዜ እንፀፀትበታለን። ምን ለማለት ነው… ለአፍንጫም ለአይንም አሁን ካለበት የተሻለ ቦታ የለም። በኢኮኖሚክሱ ሰርተህበታል ወይ ላልሺኝ፤ እርግጥ ነው ወርልድ ቪዥን ገብቼ ስራ ጀምሬ ነበር፡፡ ነገር ግን ለዚያ ቦታና ስራ የተፈጠርኩ አለመሆኔ ሲገባኝና የነፍሴ ጥሪ አርት እንደሆነ ስረዳ፣ ወደ አዲስ አበባ መጥቼ አርት ት/ቤት ገባሁ፡፡ በወቅቱ ቤተሰቤም እንጀራ ትተህ ሄደህ እንጀራ አይወጣልህም ብለውኝ ነበር፤ ደስተኞችም አልነበሩም፡፡ እኔ ግን ትዝ ይለኛል፣ ወደ አዲስ አበባ ስመጣ በኪሴ የነበረው 300 ብር ብቻ ነበር። ጫማ ጠርጌም ቢሆን የተጠራሁበትን ዓላማ አሳካለሁ የሚለውን ህልም ይዤ ነው የወጣሁት። ከዚያ አራት አመት በአርት ስኩል ትምህርቴን ስከታተል ቆይቼ፣ በፋይን አርት ዲግሪዬን አገኘሁ፡፡
በስዕል ት/ቤት በነበረህ ቆይታህ ከመደበኛው ትምህርት ውጭ በራስህ ላይ የጨመርከውን ነገር ንገረኝ…?
እንደኔ አመለካከት ትምህርት አንቺን አይፈጥርሽም ግን የተፈጠረውን አቅምሽን ቅርፅ በመስጠትና አቅጣጫ በማስያዝ ከፍተኛ እገዛ ያደርግልሻል፡፡ እኔ በተለይ ከመምህራኖቼ በጣም የሚያስገርሙ አቅሞችን አግኝቻለሁ፡፡ እነ መዝገቡ ተሰማ፣ ታደሰ መስፍን፣ ጌታሁን አሰፋ፣ በቀለ መኮንንና ሌሎችም አመለካከትን ሊቀይሩ ከሚችሉ ሰዎች ጋር የመገናኘት ዕድል ማግኘትሽ ያለሽን ነገር ጥልቀት ይጨምርልሻል፡፡ በዚህ ምክንያት ለሙያው ያለኝ ጥማት ጨርሶ ነደደ፡፡ መጀመሪያም ፓሺን ነበረኝ፤ ትምህርቱ ደግሞ የበለጠ ፍቅርና ፍላጎቱን አቀጣጠለልኝ፡፡ እርግጥ ነው መጀመሪያ ላይ የሚያሳጣሽ ነፃነት አለ…፡፡
ምን አይነት ነፃነት ነው የሚያሳጣው?
የምንማርበት ሥርዓተ ትምህርት የተቀረፀው በምዕራቡ አስተሳሰብ ላይ ማዕከል አድርጎ በመሆኑና የአገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ከግንዛቤ ውስጥ ስለማያስገባ በጣም ገዳቢ ነው፡፡ ነገር ግን አንቺ ብልህ ከሆንሽ ያንን ትምህርት ከራስሽ ሁኔታ አንፃር እየቃኘሽ መጠቀም ትችያለሽ፡፡ እኔም በት/ቤት ቆይታዬ ይህንን ሳደርግ ነው የቆሁት፡፡ ከዚያ በኋላ በነበረኝ ፍቅር… በውጤቴ ምክንያት እዚያው ት/ቤት በመምህርነት እቆያለሁ የሚል እምነት ነበረኝ፡፡ እንደው እዚያው ጨርሶ መቅረትም ባይሆን እንኳን የተወሰነ አበርክቶ ይኖረኛል የሚል ሀሳብ ነበረኝ፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ ቀረና የሀይስኩል ተማሪዎችን በራሴ ተነሳሽነት፣ ደስ ብሎኝ ስዕል ማስተማር ጀመርኩኝ። ይህን እያደረግኩኝ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ አርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የማስተማር ዕድል አገኘሁ፡፡ እዛም ለአንድ ዓመት ያህል ሰራሁ፡፡
ብዙ የስዕል አውደ ርዕዮች ላይም ተሳትፈሃል…?
አውደ ርዕዮችን--- በአሊያንስ ኢትዮ ፍራንሴዝ፣ በጎተ ኢንስቲትዩት፣ በአሜሪካ ኤምባሲና በሌሎች ቦታዎች በቡድን አቅርቤአለሁ፡፡ ይህንን ሳደርግ ግን የቀደሙ አርቲስቶች የሚሰሩትን እንደምደግም እንጂ አዲስ ነገር እንደማልሰራ ተረዳሁ፡፡ ከዚያ አንድ ህልም ይዤ ወደ ባህርዳር ሄድኩኝ፡፡ እንደምታውቂው አለ የስነ-ጥበብና የዲዛይን ት/ቤት 50 ዓመት ሞልቶታል፡፡ ከዚያ የሚወጡ አብዛኞቹ ሰዓሊዎች እዚህ አዲስ አበባ ነው የሚሆኑት። ምክንያቱም አዲስ አበባ የብዙ ኤምባሲዎች፣ የዲፕሎማቶች መቀመጫ በመሆኗ ገበያው ያለው እዚሁ ስለሆነ ነው፡፡ ወደ ክልል አይወጡም፡፡ ክልል ላይ ደግሞ በተደራጀ መልኩ የሚካሄድ የአርት እንቅስቃሴ የለም፡፡ እኔ ደግሞ ባህርዳር ያደግኩባት ከተማ ናት፡፡ ቤተሰቦቼም ያሉት እዚያው ናቸው፡፡ ስለዚህ ባህርዳር የቱሪስት ከተማ በመሆኗ አማራጭ የስነ ጥበብ ከተማ (Alternative Art corner) የማድረግ ህልም ይዤ ወደ ከተማዋ ተመለስኩኝ። እድለኛ ነኝ፤ ባለቤቴም ስራዋን ትታና ህልሜን ተከትላ አብራኝ መጣች፡፡ ከዚያም አንድ ት/ቤት ውስጥ ማስተማር ጀመርኩኝ፡፡
በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት የአርት ኮርሶችን ትሰጣለህ አይደል?
ትክክል ነው፤ አስተምራለሁ፡፡ ቅድም ያልኩሽ ት/ቤት እያስተማርኩ እያለሁ አቫንቲ ብሉናይል ሆቴል፣ አሁን ብሉናይል ሪዞርት ሆቴል ሆኖ የተቀየረው አንድ ነገር አደረገልኝ፡፡ አንድ ቀን፤ “ፈጣሪ እባክህ ያለምኩትን አሳካልኝ” ብዬ ፀሎት አደረግሁኝ፡፡ እኔ ህልሜ ታዋቂ ለመሆን አይደለም፤ ብዙ ብር ለመሰብሰብ አይደለም፤ ግን ይህ ህልሜ የእውነት መስመር እንዲይዝ እፈልጋለሁ” አልኩና ፀልዬ ወደ ነገርኩሽ ሆቴል ሄድኩኝ፡፡ ሀላፊው ሚስተር ስቴቨን ይባላል፤ አገኘሁት፡፡ በሚገርም ሁኔታ ሆቴሉ መቶ ሺህ ብር ስፖንሰር አድርጎኝ፣ 50 ያህል ስራዎችን ማቅረብ ቻልኩኝ፡፡ ካቀረብኳቸው ስራዎች ውስጥ እድለኛ ሆኜ፣ ከ20-30 ያህሉ ስዕሎች ከ2-7 ሺ ብር በሚደርስ ዋጋ ተሸጡ፡፡ በዚህ ውጤት ህይወቴን፣ ከቤተሰቤም ጋር ያለውን ነገር አስተካከልኩኝ፡፡ በርካታ ጉዳዮችን ከወንኩኝ፡፡
በዚህ መሃል የቀድሞው የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ባይሌ ዳምጤ፣ በስዕል ኤግዚቢሽኑ ስነ-ስርዓት ላይ ከባለቤታቸው ጋር ታድመው ነበርና፣ “ከተማችን እንዲህ አይነት ልጅ አለን እንዴ? ለአርኪቴክቸር ዲፓርትመንት ብዙ ጊዜ ማስታወቂያ አውጥተን አላገኘንም” ብለው ሪኮመንድ አደረጉኝ፡፡ ቅድም እንዳልሺው በዩኒቨርሲቲው ማስተማር ጀመርኩኝ ማለት ነው። ለሙያው ካለኝ ፍቅር የተነሳ ተማሪም እያለሁ፣ ሁለት ክረምቶች 80 ያህል ወጣቶችን በስዕል ትምህርት በበጎ ፈቃደኝነት አሰልጥኛለሁ፡፡  ከነዚህ መካከል ከ10 በላይ ሰልጣኞች፣ አለ የስነ ጥበብ ዲዛይን ትምህርት ቤት ለመግባት ችለዋል፡፡ ይሄም እድለኛ ነኝ ያሰኘኛል፡፡ አሁን ልጆቹ በጥሩ ሁኔታ እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ በዚህ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡
እኛ አገር ላይ ስዕል እንጀራ አይሆንም የሚለው አመለካከት በስፋት ይንፀባረቃል፡፡ አንተስ ይህን አመለካከት  ትጋራዋለህ?
ምን መሰለሽ… እንጀራ ይሆናል ብለሽ፣ እንጀራ እንጀራውን እያሰብሽ ከገባሽበት እንጀራ አይሆንም። ነገር ግን ሙያውን የእውነት ወደሺው፣ ራስሽን ሰጥተሸ ከልብሽ ስትሰሪ እንጀራ መሆን ይጀምራል። ስለዚህ ሙያችንን ወድደነው፣ በፍቅርና በትጋት ነወይ የምንሰራው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ ሙያችንን ወድደን ራሳችንን ሆነን ሥንሰራ፣ የማንንም አንገለብጥም፡፡ ስለዚህ ትኩረት እንስባለን፡፡ አሁን ሰው ለአርቱ ያለው አመለካከት እየተቀየረና አይኑ እየተከፈተ ነው። እኔ ለምሳሌ ሙያዬ በአንድ አቅጣጫ ብቻ ገቢ እንዲያመጣልኝ አልፈልግም፡፡ የህትመት ስራዎች ሰርቻለሁ፣ ዲዛይኖች ሰርቻለሁ፡፡ ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽን ካየሺው፣ የባህርዳሩንም የአዲስ አበባውንም ስዕሎች የሰራሁት እኔ ነኝ፡፡ አሁን ይህ ስራ አድካሚና እልህ አስጨራሽ ነው፡፡ 20 ሜትር በ7 ሜትር ስዕል መሳል ከባድ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ትንንሽ ብዙ ስዕሎችን መስራት ይቀላል፡፡ እኔ የማስበው ያሉኝን ነገሮች ተጠቅሜ፣ ሙያዬን ወደ ገንዘብ መቀየርና ከአንድ አቅጣጫ ጠባቂነት ራሴን ማውጣት ነው፡፡ በዚህ በኩል እድለኛ ነኝ፤ ፈጣሪ እረድቶኛል፡፡ ለምሳሌ “አርት ቴራፒ” በሚል ለጋምቢ ሆስፒታል ፕሮፖዛል አስገብቼ መልስ እየጠበቅኩ ነው፡፡
“አርት ቴራፒ” ምንድን ነው?
አንድ ታማሚ በተኛበት የሆስፒታል ክፍል ፊት ለፊቱ አንድ ማራኪ ስዕል ቢሰቀል፣ ያንን ስዕል በማየትና በመመራመር፣ ህመሙን ለአፍታ ያህል ቢረሳ ቀላል አይደለም፤ የጎንዮሽ ጉዳት የሌለው መድሀኒት ነው፤ ስለዚህ በዚህ መልኩ ስዕሎችን ሰርቼ ህመምተኞች ክፍል ለመስቀል ምክረ ሀሳብ ባህርዳር ለሚገኘው ጋምቢ ሆስፒታል አቅርቤያለሁ። ምን ለማለት ነው… ያሉትን አማራጮች ሁሉ እሞክራለሁ፤ ከማንኳኳቸው 10 በሮች አንዱ ይከፈታል፡፡
በአሁኑ ወቅት በጉራማይሌ አርት ጋለሪ “ነቁጥ” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ለዕይታ አቅርበሃል፡፡ ስራዎችህ ሁሉ የተሰሩት ደግሞ በከብት ቆዳ ላይ ነው። የስዕል (art) ፍልስፍናህ ምንድን ነው?
እንግዲህ የእኔ አርት ፍልስፍና የምለው ገና በሂደት ላይ እንዳለ ይሰማኛል፡፡ እኔ እንደ ትልቅ ነገር የማነሳው፣ በዚህኛው በ“ነቁጥ” ብቻም ሳይሆን ከመጀመሪያው አንስቶ በነበሩ ሥራዎቼ ጎልቶ የሚታይ ነገር አለ፡፡ “ተቃርኖን ማስታረቅ” የሚል ነው፡፡ ሁለት በሀሳብ፣ በቅርፅና በቀለም የሚለያዩ ነገሮች አንድ ላይ የሚሆኑበት ክፍል ፈልጎ፣ የማቀራረብና ማስታረቅ አካሄድ ነው። ለምሳሌ ኢትዮጵያ የምትባለው አገር በአስደማሚ ተቃርኖዎች የተሞላች፤ ነገር ግን ተቃርኖዎቿ ጌጥ የሆኑላት አገር ናት፡፡ ለአብነትም ዳሎል በጣም የአገሪቱ ዝቅተኛ ቦታ ነው፣ ራስ ዳሽን ከአፍሪካ በከፍታው ሁለተኛ ደረጃ  ላይ የሚገኝ ትልቅ ተራራ ነው፡፡ ሁለቱ በአንድ አገር በጣም በተቃርኖ ደግሞም ውበት ሆነው ተቀምጠዋል፡፡
ለእኔ ምዕራባዊ የሆነው አጠቃላይ ፍልስፍና “ትራዲሽናል” ሲል ያስቀኛል፡፡ ዘመናዊነት (ሞደርኒቲ) የባህላዊ ሂደቶች ቅጥያ ነው እንጂ በተለየ ሁኔታ የተፈጠረ አይደለም፡፡ ቀደም ብሎ የነበረው ባህላዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሂደት ቀስ በቀስ እየተቀየረ ይሄዳል እንጂ በአንዴ ብጥስ ብሎና ከባህላዊነቱ ተለይቶ ብቻውን የቆመ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዘመናዊነት ራሱን ለማስቀጠል አሁንም ባህላዊነት የግድ ያስፈልጋል፡፡ እኔ በስራዬ በአብዛኛው ባህላዊ ኤለመንቶችን እወስዳለሁ። በዚያው ልክ በጣም ዘመናዊዎቹንም እወስድና በጣም አስታርቄ አንድ የተጣጣመና የተቀናጀ ነገር እፈጥራለሁ። ብዙ ስራዎቼ ላይ የሚታይ ባህርይ ነው፡፡ ፈጣሪ በስራዎቹ ላይ የገለፀውም ይህንን ውበት ይመስለኛል፡፡ ይሄ ነገር ነው እንዳይሰለቸን የሚያደርገው፡፡ አሁን ቅጠል አንድ አይነት ተመሳስሎ ይኖረውና በዚያ ውስጥ ልዩነት አለው። ፋብሪኬትድ የሆነ ወይም ሰው የሰራው ነገር ነው ቶሎ የሚሰለቸው፡፡ ይሄ ከፈጣሪ የወሰድኩት ትልቅ ጥበብ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ሰው ሁሉ በፈጣሪ ሊነቃቃ ይችላል፡፡ በተፈጥሮ ብቻ ወይም በተለያየ ነገር ሊነቃቃም ይችላል፡፡ እኔ በራሱ በፈጣሪ ነው የተነቃቃሁት፡፡ እንደ አምላክ ከማምለክ በዘለለ  እንደሚጠበብ ሰው “creative-personality” አድናቂው ነኝ፡፡
“ነቁጥ” በሚል በሰየምከው  አውደ ርዕይህ ላይ ስራዎችህ ለምንድን ነው በከብት ቆዳ የተሰሩት? “ነቁጥ” ስትል የሰየምከውስ በምን ምክንያት ነው?
እኔ ወደ ቆዳ አርት የገባሁት መጀመሪያ እንደ አንድ ገጠር እንደተወለደ ልጅ፣ ከበሬና ላም ጋር ያለኝ ግንኙነትና ቅርበት የጠበቀ ነው፡፡ እንደውም አያቴ ስታሳድገኝ “ትርባልኝ” የምትባል ላም ነበረች፤ለእኔ ብቻ የተመደበች፡፡ ቀጥታ አፌን ከፍቼ፣ አያቴ ወተት አፌ ላይ እደረገች ነው ያሳደገችኝ፡፡ ከዚህ አለፍ ብዬ በሬን መመልከት ጀመርኩ፡፡ በሬ እየተገረፈ አርሶ ያበላል፣ ከዚያ ስጋውን ይሰጣል፡፡ ቆዳውን ለገመና መሸፈኛ ይሰጣል፡፡
በመፅሐፍ ቅዱስ አማኒያን ዘንድ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰው በሀጢያቱ ምክንያት ፀጋውን ተገፍፎ፣ ራቁቱን ሲቀር ገመናው ለመሸፈን የተጠቀመው ቅጠል ነው። ነገር ግን ቅጠል ረጅም ጊዜ ስለማይቆይ ጌታ ራሱ ቆዳ ነው የሰጣቸው፤“ለምድ አለበሳቸው” ይላል፡፡ ቀንዱን ለመጠጫ፣ ጅራቱን ለመግረፊያ እንጠቀማለን፡፡ በፖለቲካዊ አንድምታም ከሄድን፣ ነጋሪት ተጎስሞ አዋጅ የሚነገረው ከበሬ ቆዳ ተሰርቶ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እበቱ ራሱ ማገዶ ይሆናል፡፡
በሬ ቁርጥምጥም አድርገን የምንጠቀመው ፍጥረት ነው፡፡ ለዚህ ሁሉ ፈቃደኛ የሆነም ነው፡፡ ይህ ነው መነሻዬ፤ ቆዳ ላይ ያተኮርኩበት፡፡ በሬ ያ ሁሉ ቆዳው ላይ ያለ ዥንጉርጉር፣ ትልቅም ይሁን ትንሽ ነቁጥ፣ ብዙ በሬ አያደርገውም፤ እነዛ ተባብረው ነው በሬ የሚያሰኙት፡፡ ይህ እሳቤ የበለጠ ስለሳበኝ ነው ያተኮርኩበት፡፡
በተለይ በገጠር አካባቢ ቆዳ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ነው ያለው---
እውነት ነው፡፡ የገጠሩ የቆዳ አጠቃቀም ከተነሳ አይቀር በጣም የሳበኝ፣ አጎዛውን ግድግዳ ላይ ሰቅለው፣ ለጌጥና ለአይን ማረፊያ ያደርጉታል፡፡ ከዚያ ያወርዱና አንጥፈው ይተኙበታል፡፡ ሲተኙ ደግሞ ያሸትቱታል፡፡ እነዚህ የውበት ልምምዶች ሁለት አይነት ነገር አላቸው፤ ተግባራዊም ውበታዊም። እነዚህን ሁለት መልክ ያላቸው ስራዎች ለእይታ ማቅረብ በምዕራባዊያን አረዳድ፤ “ማቴሪያል ካልቸር” ነው የሚሉት፡፡ ምን ማለት ነው? ሰው ለዕለት ተዕለት ኑሮው የሚጠቀምባቸው እንጂ የተጠበበት አርት አይመስላቸውም፡፡ እንደኔ እምነት ግን ሙዚየም ባለማቅረባቸው እንጂ እነዚህ ስራዎች በምዕራባዊያን ሙዚየሞች ከሚታዩ ስዕሎች በላይ ጠንካራ ናቸው፡፡
እንደውም አሁን በዘመናዊ ስነ-ጥበብ ትልቁና ጠንካራ መሆን አለበት የሚባለው አርቲስቱ በአይን ታይቶ ከሚያበቃና ዋው ከሚያስብል ስራ በዘለለ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የሆኑ ጉዳዮችን የሚያነሳ፣ የሚቀሰቅስና የሚታገል ነው። እነዚህ አርቲስቶች ከእለት ተእለት ህይወታቸው ጋር የተቆራኙ ነገሮችን ወስደው ለታይታና ለእይታ ብለው ሳይሆን ከልብ የመነጨ ሀሳባቸውን ያንጸባርቁባቸዋል፡፡ ለነዚህ ስራዎች ደግሞ ቦታ ተሰጥቶ መካተት አለባቸው የሚል ሀሳብ ይዤ  ነው የተነሳሁት፡፡
ታዲያ ስራዎችህ ተቀባይነት አግኝተውልሃል?
አሁን ይሄን የሚደግፉልኝ ሱዛን ፎግል፣ ካሮል ዳንከል እና ሌሎችም ፀሀፊዎች አሉ፡፡ እነዚህ ፀሀፊዎች የአፍሪካዊያን አርት በምዕራባዊያን ሙዚየም ለእይታ ሲቀርብ እንደ እቃ ነው የሚከለኮለው እንጂ እንደ ሪፋይን አርት በስርዓቱና በክብር አያቀርቡትም፡፡ የራሳቸውን ግን ከአምላክና ከሰማይ የወረደ አድርገሽ እንድትመለከቺው፣ ያንን ስሜት ይፈጥሩብሻል፡፡ እኔ እንደምታዪው፤ እነዚህን ሞሰቦች፣ አገልግሎችና ሌሎች እቃዎችን ከእቃነት በዘለለ ራሳቸው ጥልቅ የሆነ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እሳቤ ያላቸው መሆኑን ለማሳየት ሞክሬያለሁ፡፡ ቅድም የጠቀስኩልሽ ፀሀፊዎች፣ይህንን ስራና አስተሳሰብ ይደግፉታል፤ተቀባይነቱ የሚያጠራጥር አይደለም፡፡
በአውደ ርዕዩ ላይ ከቀረቡት መካከል የገረመኝ፣ ትልቁ በቆዳ የተለበጠው መሶብ፣ በቁልፍ ተቆልፎ በርካታ የቁልፍ መክፈቻዎች ከበውታል፡፡ እስቲ የዚህን መሶብና የቁልፍ መክፈቻዎቹን ምስጢር አብራራልኝ?
በዚህ መሶብና በቁልፉ ማስተላለፍ የፈለግኩት እንጀራ፣ ተስፋና ዕድልን ነው፡፡ የእቃዎቹን አቀራረብ installation (ኩልኩል) እንለዋለን። ጥልቅ የሆነውን የሰው ህይወትና በሕይወቱ የሚገጥሙትን ጉዳዮች ሊገልፅ በሚችል መንገድ የምናስቀምጥበት ነው:: ሰው ተስፋ አለው፣ ዕድልም አለው፣ እንጀራም አለው፡፡ ተስፋው ያለ ማቋረጥ ይሄንን ቁልፍ ለመክፈት እንዲሞክር ያደርገዋል። ዕድሉ ሙከራውን ያሳካለታል፡፡ እንጀራው በነዚህ ሂደቶች የሚገኝ ስኬት ነው፡፡ ይህ የተቆለፈ መሶብ በስሩ ከተደረደሩት መዓት ቁልፎች አንዱ ይከፍተዋል። የሚከፍተው ቁልፍ ምንም ምልክት የለውም፡፡ ይሄ የብዙ ሰዎችን ሀሳብ ይሞግታል፡፡
በምን መልኩ?
ቁልፉ ከእነዚህ ቁልፎች መሀል እንዳለ እናውቃለን። የሰው ልጅ ከእነ ዕድሉ፣ ከእነ ስጦታው ነው የተፈጠረው፤ ነገር ግን አብዛኛው የሚሞክርና የሚጥር አይደለም፡፡ አንድ ሰው ተስፋ ካደረገ፣ ከጣረ ዕድሉ ቁልፉን እንዲያገኝ ያደርገዋል። ይሄ ሙግት በውስጥሽ መመላለሱ አይቀርም፡፡
ለጉብኝት የሚመጡ ሰዎችን የዚህን ሞሰብ ቁልፍ ሞክረው እንዲያገኙ ስትጋብዝ አይቻለሁ። እኔም በርካታ ቁልፎችን ሞክሬ መሶቡን መክፈት አልቻልኩም፡፡ ለመሆኑ እስካሁን ሞክሮ የተሳካለትና የከፈተው አለ?
የሚገርምሽ አንድ ልጅ ሞክሮ ተሳክቶለታል፡፡ በውስጡ ምን አገኘ የሚለውን አሁን አልናገረም፤ ነገር ግን ይሄ ልጅ መክፈት አለብኝ ብሎ ቆርጦና ወስኖ ነው የተቀመጠው፡፡ ልጁ ምን ያህል ሰዓት  ታግሶ ወስኖ እንደተቀመጠ ስመለከት፣ የልጁ ቁርጠኝነት ለብዙ ሰው ትምህርት የሚሆን ነው። ህፃናትም በብዙ ትዕግስት ፈልገው ፈልገው፣ “እባካችሁ የትኛው ነው፣ አሳዩን?” እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡
አንተ ግን ቁልፉ የትኛው እንደሆነ ታውቀዋለህ?
በፍፁም! እኔም አላውቀውም፡፡ አንድም የሌላው ህብረተሰብ አካል ለመሆን፣ በሌላም በኩል ለራሴ እንዳላዳላ በሚል አላውቀውም፡፡ እንግዲህ በምዕራቡ ዓለም ስዕል በእጅ አይነካም፤ አይዳሰስም፤ በቃ ሀይማኖታዊ ነገር አድርገው ነው የሚያስቀምጡት። አምስት ሜትር ከስዕሉ ርቀሽ ነው የምትመለከቺው። እኛ ጋ ትነኪዋለሽ፣ ትዳስሺዋለሽ፣ የሰቀልሺውን ራሱ አውርደሽ ትተኚበታለሽ፤ ስለዚህ የሚዳሰስ የሚታይና የሚሸተት ሥራ ነው የምንሰራው፡፡
አውደ ርዕዩን ብዙ የውጭ ዜጎች ሲጎበኙት ተመልክቻለሁ፡፡ ጎብኝዎች የሰጡህ አስተያየት ምን ይመስላል?
ያገኘኋቸው ሁሉ በጣም ፍላጎት ያሳደረባቸው ነገር ምን መሰለሽ? ወይ ዘመናዊነቱ ውስጥ ጥልቅ ብለህ አልገባህ ወይ በጣም ባህላዊ በሚባል መንገድ አልመጣህ፤ ሁለቱን አቻችለህ ስለምትሞግተን እኛም የሀሳብ ለውጥ ለማድረግ ተመችቶናል፡፡ በሌላ በኩል በአይን ከመታየት አልፎ እንድንነካ፣ አገላብጠን እንድናይ ዕድል አግኝተናል፡፡ የሚዳሰስ የሚሸተት የሚታይ ስዕል ማየታችን አዲስ ስሜት ፈጥሮብናል ሲሉ  ተናግረዋል፡፡
ሌላ መናገር የምፈልገው ነገር፣ በምዕራባዊያን ፕላት ፎርም ውስጥ የተካተተው የስነ- ጥበብ ፍልስፍና እና ታሪክ የሌላውን አለም ያላቀፈ ነው የሚል ሙግት አለ። እነ ፒካሶ በተነሱበት ዘመን በተጓዳኝ በአፍሪካ፣ በላቲን አሜሪካ፣ ከምዕራቡ ተመጣጣኝ የሆኑ የአርት ክንውኖች የነበሩ ቢሆንም የተካተተው የምዕራቡ ብቻ ነው የሚል የሀሳብ ፍጭት ስላለ፣ በዚያ ሙግት ውስጥ የእኔን ትንሽ ነፀብራቅ ለማሳየት ነው እየሞከርኩ ያለሁት፡፡
በስዕሎቹ በቆዳ የተለበጠ ቴሌቪዥን ተመልክቻለሁ። ትርጉሙ ምንድን ነው?
ቴሌቪዥን በአገራችን የማህበረሰብን ስትራክቸር የቀየረ ነው፡፡ ምን ማለት ነው--- ቀደም ባለው ጊዜ ቤት ውስጥ ስንቀመጥ፣ ትልልቅ ሰዎችን ከብበን ነበር፡፡ ማዕከል የሚሆኑት እናት አባቶቻችን ናቸው። አሁን ደግሞ ቴሌቪዥን ከበን ነው የምንቀመጠው፡፡ የቴሌቪዥኑ አቀማመጥ ደግሞ ለሁሉም ለህፃን ለአዋቂው እንዲመች ተደርጎ ነው የሚዘጋጀው፡፡ ዱሮ ተረት፣ ምክር የምንሰማው ከታላላቆቻችን የሚጠቅመንን ብቻ ነበር፡፡ አሁን ቴሌቪዥን የምናየው ያለ ዕድሜ ገደብ ነው፡፡ ለልጅ ነው ለአዋቂ ነው የለም፣ ያውም ተገምግሞ በማያልፍ የትኛውም ሀሳብ ውስጥ አብረን እንሰለፋለን፡፡ ይሄ ለእኔ አስጊ ነው፡፡ ቴሌቪዥኑን ቆዳ ያለበስኩት፣ ከቴሊቪዥኑ የሚወጣውን እኛ ብናስተካክለውና ብንዋጀው የሚል ምኞቴን ለማስተላለፍና የሚጠቅመንን ብቻ የምንሰማበት ልናደርገው ብንችል የሚለውን ህልሜን ለማሳየት ነው፡፡ እንግዲህ የሀሳብ ተቃርኖውን የሚያሳይ ነው። ቆዳው የእኛ ነው፤ ቴክኖሎጂው የእነሱ ነው። ይሄ በእጄ የያዝኩት ስልክ ጥሩም መጥፎም አይደለም፤ በስልኩ የምጠቀምበት ነገር ነው ጥሩና መጥፎ ሊያሰኘው የሚችለው፡፡ በስልኩ ደውዬ “ሰው ግደል ወይም የወደቀ ሰው አንሳ” ስል ውጤቱ ይወሰናል ማለት ነው፡፡
አሁን ደግሞ በአሜሪካ ስላሳየኸው አውደ ርዕይ  እና በቅርቡ በግብፅና በኢኳዶር ስለምታሳየው የስዕል አውደ ርዕይ አጫውተኝ ----
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ፣ አንድም ቀን ታዋቂ ለመሆን ብዬ ከአርት ጋር ተቆራኝቼ አላውቅም፤ ነገር  ግን በፍቅርና በፍላጎት ተሞልተሽ ስትሰሪ፣ አይን ውስጥ ትገቢያለሽ፡፡ በመጀመሪያ ያገኘሁት እድል በአሜሪካ ላስቬጋስ በኔቫዳ ዩኒቨርሲቲ የሚገኝ የስነ-ጥበብ ተቋም ነው፡፡ በማይመች አካባቢ ውስጥ ሆኜ በባህርዳር ለአምስት ዓመታት ሥነ-ጥበብ ላይ በመስራቴ በተለይም ከወጣሁበት አካባቢ ሀይለኛ ግንነት ያለው ስራ መፍጠር በሚል “ፐብሊክ ሌክቸር” ሳደርግ፣ በተጨማሪም ስራዎቼን “ባሪክ” ሙዚየም ውስጥ ከንግግሬ ጎን ለጎን ለእይታ አቅርቤ ነበር፡፡ ከዚያም ለሶስት ሳምንታት ያህል ግራንት ሆል ጋለሪ ሆል ውስጥ ስራዎቼ ለእይታ በቁ፡፡ ቦልደርሲቲ በሚባል ከተማም ስራዎቼ ለህዝብ ለእይታ በቁ፡፡ በዚያው ከተማም ለህዝብ ንግግር አድርጌአለሁ። ይሄ በጣም ያስደሰተኝ ኢትዮጵያን የማያውቁ ሰዎች ገጥመውኝ ነበር፡፡ በእኔ ስራ ምክንያት ኢትዮጵያን ማወቃቸው ትልቅ ደስታ ፈጥሮብኛል፡፡ እነ ኃይሌ ገ/ሥላሴን እያወቁ ኢትዮጵያን አያውቁም፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ስለ ኢትዮጵያ መናገሬ ያስደስተኛል። እርግጥ ነው ስሄድ አበባ ይዞ የተቀበለኝ የለም፤ የሰራኋቸውን ለእይታ ያቀረብኳቸውን ስራዎቼን ብዙ ግምት ውስጥ ያስገባ የለም፤ ሆኖም ኢትዮጵያን አስተዋውቄያለሁ፡፡ እርግጥ ሲጠሩኝ ከወጣሁበት አካባቢና ባህል ጋር የተቆራኘ ሥራ በመስራቴ ሁኔታዎች በማያበረታቱበት ድባብ፣ በፈተና ውስጥ ያለማቋረጥ የስዕል አውደ ርዕይ ለአምስት ዓመት በማቅረቤ ነው፡፡ በባህርዳር በቆየሁባቸው በነዚህ ጊዜያት አመታዊ አውደ ርዕዮች እንዲኖሩ አድርጌያለሁ፡፡
ሁለቱ ላይ በተለይ የአዲስ አበባ አርቲስቶች እንዲሳተፉ በማድረግ፣ ባህርዳርን አማራጭ የስነ-ጥበብ ማዕከል የማድረግ ህልሜን ለማሳካት ሙከራዬን የጀመርኩበት ነው፡፡ “ጥበበ ባህርዳር” “አርት ኦፍ ዘ ናይል” በተሰኙ ኤግዚቢሽኖች ነው ይህን የሰራሁት። በኋላም በግሌ ሦስት ኤግዚቢሽኖች አቅርቤያለሁ፡፡ በብሔራዊ ሙዚየምም “ሀገረ ቀለም ኢትዮጵያ” የተሰኘ በሀሳብም፣ በቴክኒክም ሆነ በቀለም በዛና ተለቅ ያለ ኤግዚቢሽን ነበረኝ። አሁን በሶሻል ሚዲያም በርትቼ እየሰራሁ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎችም በኔ ተነቃቅተው እየፃፉ ይገኛሉ። ናይጄሪያ በሚታተም “ታይምስ” የተሰኘ መፅሄት ላይ “ዘ አርቲስት ኦፍ ናሽናል ኮንሺየስነስ” በሚል ርዕስ ሽፋን አግኝቻለሁ፡፡
በግብፅና በኢኳዶር ስለምታቀርበው አውደ ርዕይ ንገረኝ---?
በኢኳዶር የሚካሄደው ዓለም አቀፍ ሰሚት ነው። በግብፅ ደግሞ “ኢንተርናሽናል አርት ሲምፖዚየም” ከአፕሪል 12 እስከ 24 ቀን 2018 ይካሄዳል፡፡ በዚያ ላይ እሳተፋለሁ፡፡ በዚህ ሁሉ ደስኛ ነኝ፡፡ አገራችን የ3 ሺህ ዓመት ታሪክ ያላትና የባህልና ታሪክ አገር መሆኗ፣ ለአንድ የፈጠራ ሰው በተለይ በስነ-ጥበብ ሙያ ውስጥ ላለ ሰው እድለኝነት ነው፡፡ ብዙ የምንሰራበት እድል አለ፡፡ ህልሜ ስዕልን ለእይታ አቅርቦ ከመሸጥ በዘለለ ጠንካራ ንቅናቄ ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ ደግሞ ይሳካል፡፡  


Read 2725 times