Tuesday, 20 March 2018 11:35

የአርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያምን ህይወት ለመታደግ ጥሪ ቀረበ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

· የደም ዓይነቱ A እና O የሆነ ኩላሊት ለጋሽ ይፈልጋል
         · ለአርቲስቱ ገቢ ለማሰባሰብ የባንክ አካውንት ተከፍቷል
         · ከቤተሰቡ ኩላሊት ለመለገስ የተደገረው ሙከራ አልተሳካም
              ናፍቆት ዮሴፍ

    ከ40 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ ኪነ- ጥበብ የማይተካ ሚና ሲጫወት የቆየው የመድረክ ፈርጥ አርቲስት ፍቃዱ ተክለማሪያም ሁለቱም ኩላሊቶቹ ከጥቅም ውጪ በመሆኑ ሳቢያ ህይወቱን ለመታደግ የሚያስችል የድጋፍ ጥሪ ቀረበ፡፡ ባለፈው ሐሙስ አርቲስቱን ለመታደግ የተቋቋመው ኮሚቴ በአፍሮዳይት ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ የኢትዮጵያ ህዝብ የአርቲስቱን ነፍስ ለማዳን እንዲረባረብ ጥሪ የቀረበ ሲሆን ጉዳዩ ለህዝብ ይፋ ሳይሆን ከቤተሰቡ በሚለገስ ኩላሊት ህክምና ሊያደርግ የነበረው ሙከራ ከለጋሾቹ የጤና ሁኔታ ጋር በተያያዘ ሳይሳካ መቅረቱ ተገልጿል፡፡
አርቲስቱ “ገንዘብ አትለምኑ ህዝብ አታስቸግሩ፤ የሙያውም ክብር አይደፈር፤ እኔም ከነክብሬ ልሙት” በማለት ጉዳዩ ለህዝብ ይፋ ሆኖ ገንዘብ እንዳይሰበሰብ አጥብቆ መጠየቁን የገለፁት የኮሚቴው አባላት፤ ምንም እንኳን አርቲስቱ ባይደግፈው አይናችን እያየ አርቲስቱን ማጣት ስለሌለብን ጉዳዩን ለህዝብ ይፋ አድርገነዋል ብለዋል፡፡
የአርቲስቱ ሁለቱም ኩላሊቶች ሥራ ለማቆም ጥቂት ጊዜ እንደቀራቸው የተነገረ ሲሆን ወደ ዲያሊስስ ሳይገባ በፊት በውጭ አገር በጥሩ ህክምና የኩላሊት ንቅለ ተከላ እንዲደርግ አስፈላጊውን እገዛ በማድረግ ያገለገለው ህዝብ የአርቲስቱን ውለታ እንዲመልስ ጥሪ ቀርቧል፡፡
ህዝቡ በመጀመሪያ በፀሎት እንዲያግዘውና ከዚያም የኩላሊትና የገንዘብ ልገሳ እንዲያደርግለት ተጠይቋል፡፡
“አርቲስቱ ሙሉ በሙሉ ኩላሊቱ ስራ አቁሞ አልጋ ላይ ተኝቷል፡፡” እየተባለ የሚነገረው ፍፁም ሀሰት እንደሆነ የገለፁት የኮሚቴው አባላት፤ አርቲስቱ አሁንም በስራ ላይ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
የኮሚቴ አባላቱ አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ፣ ሀይሉ ከበደ፣ መቅደስ ፀጋዬ፣ ቴዎድሮስ ተስፋዬ፣ ውድነህ ክፍሌና መሰረት መብራቴና ወዳጁ ሳሙኤል ብርሃኔ ሲሆኑ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አጎዛ ቅርንጫፍ የተከፈተው የገቢ ማሰባሰቢያው የባንክ ቁጥር 1000239345488 በአርቲስት መሰረት መብራቴ፣ በመቅደስ ፀጋዬና በሳሙኤል ብርሃኔ ስም ተከፍቶ ስራ መጀመሩም በዕለቱ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል በውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን አርቲስቱን ሊረዱ የሚችሉበት “Go fund me” አካውንት በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ስም የተከፈተ ሲሆን በዚህ አካውንት “Please help save Fekadu” ብለው በመግባት የበኩላቸውን እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል፡፡ ከዚህ አካውንት 75 ሺ ዶላር የሚጠበቅ ሲሆን ከተከፈተ ጀምሮ 2015 ዶላር ገቢ መደረጉን አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ተናግሯል፡፡
ለህክምና ምን ያህል ወጪ እንደሚያስፈልግውና በአገር ውስጥ የኩላሊት ንቅለ ተከላ በስኬት እየተካሄደ ወደ ውጭ አገር ሄዶ መታከም ለምን አስፈለገ በሚል ለተነሳው ጥያቄ፣ አርቲስቱ ከስኳርና ከሌሎች የጤና ችግሮች ጋር በተያያዘ ህክምናው ውስብስብ በመሆኑ እንዲሁም ኩላሊቶቹ መቀየር እንዳለባቸው ቀድሞ የተደረሰበት በመሆኑ ከአገር ውስጥ ይልቅ ውጭ በተሻለ ቴክኖሎጂና ህክምና ንቅለ ተከላ ቢያደርግ እንደሚሻል በመነገሩ፣ የግድ ውጭ ሄዶ መታከም እንዳለበት ተወስኗል ተብሏል። የህክምናውን ወጪ በተመለከተ በተለያዩ አገራት የተለያዩ የገንዘብ መጠኖች መገለፃቸውንና ለአርቲስቱ ህክምና የሚወጣው ወጪ እንደሚገኘው የህዝብ ድጋፍ እንደሚወሰን ተገልጿል፡፡ በየትኛውም ሁኔታ ግን የተሻለውን ህክምና እንዲያገኝ እስከ መጨረሻው ጥረት እንደሚደረግ የገለፁት የኮሚቴው አባላት፤ በቀጣይ የገቢ ማሰባሰቢያ የኪነ-ጥበብ ፕሮግራሞች እንደሚካሄዱ፣ በየደረጃውም ይፋ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ በርካታ አንጋፋና ወጣት የኪነ-ጥበብ ሰዎች የተገኙ ሲሆን አርቲስት ደበበ እሸቱ፣ አረጋኸኝ ወራሽ፣ አብራር አብዶ፣ ወለላ አሰፋ፣ ፍቅርተ ጌታሁን፣ ሽመልስ አበራ፣ ዳዊት ፍሬው፣ ሀይሉ ሶፊ እና ሌሎችም ተገኝተዋል፡፡
“ሞት በኩላሊት ይብቃ” የተባለ ማህበር ፕሬዚዳንት የሆኑትና የኩላሊት ህመምተኛው አቶ ኢዮብ ዳዊት በሰጡት አስተያየት፤ “የእውቁ አርቲስት የኩላሊት ህመም በኢትዮጵያ በየጥጋጥጉ በኩላሊት ህመም ለሚሰቃዩ ትንሳኤ ነው” ያሉ ሲሆን ይህ ኮሚቴ አርቲስቱ ከዳነ በኋላ ስራውን በመቀጠልና አርቲስቱንም አምባሳደር በማድረግ ለሌሎች ህሙማን እንዲተርፍና የኩላሊት ህክምና ሆስፒታል እስከማሰራት ጥረት እንዲያደርጉ ለኮሚቴው አባላት ጥሪ አቅርበዋል፡፡

Read 2938 times