Tuesday, 20 March 2018 11:32

የአለማችን ፖለቲከኞችና ዝነኞች በፊዚክሱ ሊቅ ስቴፈን ሃውኪንግን ሞት አዝነዋል

Written by 
Rate this item
(9 votes)

የዘመናችን የፊዚክስ ሊቅ ፕሮፌሰር ስቴፈን ሃውኪንግ በተወለደ በ76 አመቱ ባለፈው ረቡዕ ከዚህ አለም በሞት መለየቱን ተከትሎ፣ የእንግሊዟን ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይን ጨምሮ በርካታ የአለማችን መሪዎች፣ ሳይንቲስቶች፣ አርቲስቶችና ተቋማት የተሰማቸውን ሃዘን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ፡፡
ስቴፈን ሃውኪንግ ለአለማችን ሳይንስ እጅግ የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከተና ስለ ህዋው ያለንን እውቀት በማዳበር ረገድ አለማቀፍ አስተዋጽኦ ያበረከተ ታላቅ ሰው ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ፤ ሳይንቲስቱ በመላው አለም ለሚገኙ በርካታ ዜጎች የመንፈስ መነቃቃት ምንጭ እንደነበር በማስታወስ በሞቱ የተሰማቸውን ሃዘን ገልጸዋል፡፡
የአሜሪካው የጠፈር ተቋም ናሳ በትዊተር ገጹ ላይ ባሰፈረው የሀዘን መግለጫ፤ ስቴፈን ሃውኪንግ ታላቅ የፊዚክስ ሊቅና የሳይንስ አምባሳደር ነው። የአእምሮው ውጤት የሆኑት ንድፈ ሃሳቦች፣ በዕድሎች ወደተንበሸበሸ ህዋ እንድንገባ በር የከፈቱ ናቸው ሲል የሳይንቲስቱን የላቀ አስተዋጽኦ በክብር ዘክሯል፡፡
የአውሮፓ የጠፈር ተቋም በበኩሉ፤ ስቴፈን ሃውኪንግ ህልማችንን እውን ከማድረግ የሚገታን አንዳች ሃይል እንደሌለ ያሳየን መንገድ መሪያችን ነው ሲል ያወደሰው ሲሆን የጎግል ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰንዳር ፒቻይ በበኩላቸው፤ አለማችን የላቀ አእምሮና እሳት የላሰ ሳይንቲስት አጣች ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ ስቴፈን ሃውኪንግ በምርምር ስራዎቹ ለሳይንስ እድገትና ለአለማችን ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል በማለት እማኝነታቸውን የሰጡ ሲሆን፣ ኬቲ ፔሪ፣ ሻሮን ስቶን እና ጂም ኬሪን ጨምሮ በርካታ የሆሊውድ ዝነኞችና ድምጻውያንም ለሳይንቲስቱ ያላቸውን አክብሮት በተለያዩ መንገዶች ገልጸዋል፡፡
ታዋቂ የአለማችን የጠፈር ተመራማሪዎች፣ ሳይንቲስቶችና የዩኒቨርሲቲዎች ፕሮፌሰሮች የሃዘን መግለጫቸውን ያወጡ ሲሆን ካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ በርካታ የእንግሊዝና የሌሎች አገራት ዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት ስቴፈን ሃውኪንግንና በሳይንሱ ዘርፍ ያበረከታቸውን አስተዋጽኦዎች የሚዘክሩ የተለያዩ ዝግጅቶችን ማከናወናቸውንም ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡


Read 7992 times