Print this page
Sunday, 18 March 2018 00:00

እንግሊዝና ሩስያ በኬሚካል በተመረዙት ሰላይ ጉዳይ ተካርረዋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ባለፈው እሁድ ሳላበሪ በተባለቺው የእንግሊዝ ከተማ ውስጥ በአደገኛ ኬሚካል በተፈጸመባቸው ጥቃት በጽኑ በታመሙትና በሆስፒታል በሚገኙት የቀድሞው የሩስያ ሰላይ ሰርጌይ ስክሪፓልና ሴት ልጃቸው ዩሊያ ስክሪፓል ጉዳይ ሲወዛገቡ በሰነበቱት እንግሊዝና ሩስያ መካከል የተፈጠረው ፍጥጫ መካረሩንና ወደ ዲፕሎማቲካዊ እርምጃ መሸጋገሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በሰውየው መመረዝ ላይ የሩስያ እጅ ሊኖርበት ይችላል የሚል አቋም የያዘቺው እንግሊዝ፤ ሰውዬው የተመረዙት ሩስያ ሰራሽ በሆነው ‘ኖቪቾክ’ የተሰኘ ገዳይ ኬሚካል መሆኑን በመጥቀስ፣ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንድትሰጥ ለሩስያ ያቀረበቺው ጥያቄ ምላሽ አለማግኘቱን ሰበብ በማድረግ፣ ባለፈው ማክሰኞ 23 የሩስያ ዲፕሎማቶችን በአንድ ሳምንት ውስጥ ከአገሯ እንዲወጡ ያዘዘች ሲሆን፣ በጉዳዩ ላይ እጃችን የለበትም ሲሉ ያስተባበሉት የሩስያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርም፤ አገራቸው ተመሳሳይ አጸፋ እንደምትሰጥ ማስታወቃቸው ተዘግቧል፡፡
የፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ አሜሪካና እንግሊዝ መሪዎች ባለፈው ረቡዕ ባወጡት የጋራ መግለጫ፣ በቀድሞው የሩስያ ሰላይ ላይ የተፈጸመው የኬሚካል ጥቃት አይነት ከሁለተኛው የአለም ጦርነት በኋላ በአውሮፓ የተፈጸመ የመጀመሪያው ጥቃት መሆኑን አስታውሰው፣ ድርጊቱ በእንግሊዝ ሉአላዊነት ላይ የተፈጸመ አደገኛ ጥቃት በመሆኑ በአጽንኦት እንደሚያወግዙት አስታውቀዋል፡፡
በቀድሞው ሰላይ ላይ የተፈጸመው ጥቃት የኬሚካል ጦር መሳሪያዎች ስምምነትንና አለማቀፍ ህጎችን የሚጥስ ህገወጥ ድርጊት ነው ሲሉ ያወገዙት አገራቱ፤ የሩስያ መንግስት በሰላዩ ላይ የተፈጸመውን ጥቃትና ተመርዘውበታል የተባለው ገዳይ ኬሚካል እንዴት ከእጇ ወጥቶ አውሮፓ ተሸግሮ ለጥቃት ሊውል እንደቻለ በቂና ዝርዝር መግለጫ እንድትሰጥም አገራቱ በጋራ መግለጫቸው ጠይቀዋል፡፡
የቀድሞው የሩስያ ሰላይ ሰርጌይ ስክሪፓል የ33 አመት ዕድሜ ካላት ሴት ልጃቸው ጋር ባለፈው እሁድ ሳልስበሪ ከተማ በሚገኝ የገበያ መደብር ውስጥ ራሳቸውን ስተው ወድቀው መገኘታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ሁለቱም በጠና ታመው በሆስፒታል ህክምናቸውን እየተከታተሉ እንደሚገኙም አመልክቷል፡፡
የ66 አመቱ የቀድሞ የሩስያ ሰላይ ስክሪፓል እ.ኤ.አ በ2004 ለእንግሊዙ የስለላ ተቋም ኤምአይሲክስ ሚስጥራዊ መረጃ አሳልፈው ሰጥተዋል በሚል በሩስያ መንግስት ክስ ተመስርቶባቸው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ በ2010 በአሜሪካና በሩስያ መካከል የሰላዮች ልውውጥ መደረጉን ተከትሎ፣ ግለሰቡ በእንግሊዝ ጥገኝነት አግኝተው በዚያው ሲኖሩ እንደነበርም ጠቁሟል፡፡

Read 2221 times
Administrator

Latest from Administrator