Sunday, 18 March 2018 00:00

“የሞያሌ ግድያ በስህተት የተፈፀመ አይደለም” ያሉት ባለስልጣን ታሰሩ

Written by 
Rate this item
(14 votes)

“በሞያሌ የተፈፀመው ግድያ በስህተት አይደለም” ያሉት የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደኦ፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጠዋት፣ በኮማንድ ፖስት ተይዘው መታሰራቸው ታውቋል፡፡
አቶ ታዬ ባለፈው ቅዳሜ በሞያሌ ከተማ 10 ሰዎች በመረጃ ስህተት በሚል በመከላከያ ሃይል ሰራዊት ተተኩሶ መገደላቸውን ተከትሎ ለቪኦኤ እና ለጀርመን ድምፅ ራዲዮ በሰጡት መግለጫ፤የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ ግድያው በመረጃ ስህተት የተፈፀመ ነው ብሎ እንደማያምን ማስታወቃቸው  አይዘነጋም፡፡
ኃላፊው በመግለጫቸው ግድያውን ፈፅመዋል በሚል በቁጥጥር ስር የዋሉት የመከላከያ ሰራዊቱ አባላት፣ በወታደራዊ ፍ/ቤት ይዳኛሉ መባሉን በመቃወም፣ ህዝብ በግልፅ ሊከታተለው በሚችለው የክልሉ መደበኛ ፍ/ቤት ጉዳያቸው መታየት አለበት ሲሉም ተከራክረዋል፡፡  
አቶ ታዬ ደንደኦ ሐሙስ ጠዋት አዲሱ ገበያ አካባቢ ከሚገኘው መኖርያ ቤታቸው፣ ወደ ቢሮአቸው ሲያመሩ፤ በፌደራል ፖሊስ አባላት መያዛቸውን የአይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ አቶ ታዬ ሲታሰሩ የአሁኑ ለሦስተኛ ጊዜ መሆኑን የሚገልጹት ምንጮች፤ከዚህ ቀደምም ለ3 ዓመትና ለ7 ዓመታት መታሰራቸውን ያስታውሳሉ፡፡   
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈፀሚያ መመሪያ፤የክልል መንግስታት የኮሙኒኬሽን ኃላፊዎችና ባለስልጣናት በጸጥታ ጉዳዮች ላይ መግለጫ እንዳይሰጡ የሚከለክል መሆኑ ይታወቃል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከታወጀ ወዲህ በኦሮሚያ ክልል አቶ ታዬ ደንደኦን ጨምሮ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን የአድማ በታኝ ኃይል አዛዥ፣ የነቀምት ከተማ ከንቲባ፣የምስራቅ ወለጋ ዞን ም/አስተዳዳሪና የከለም ወለጋ ወረዳ ፍትህ ቢሮ ሃላፊ በኮማንድ ፖስቱ መታሰራቸውን ምንጮች ይናገራሉ፡፡
እስካሁን በኮማንድ ፖስቱ ማንና ምን ያህል ግለሰቦች እንደታሰሩ ያልተገለጸ ሲሆን የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ለመቆጣጠር በፓርላማ አባላት የተቋቋመው የምርመራ ቦርድ፣በሚቀጥለው ሳምንት መጀመሪያ ላይ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የታሰሩትን አካላት ስም ዝርዝር  ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡   

Read 7724 times