Tuesday, 13 March 2018 13:19

ጄፍ ቤዞስ የአለማችን ቁጥር አንድ ቢሊየነር ሆነዋል

Written by 
Rate this item
(3 votes)

የአለማችን ቢሊየነሮችን የሃብት ደረጃ በማውጣት በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤ የ2018 የፈረንጆች ዓመት የአለማችንን ቀዳሚ ቢሊየነሮችን ዝርዝር ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ያደረገ ሲሆን የ112 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ያስመዘገቡት የአማዞን ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጄፍ ቤዞስ በቀዳሚነት ተቀምጠዋል።
ቤዞስ አምና ከነበራቸው አጠቃላይ ሃብት ዘንድሮ የ39.2 ቢሊዮን ዶላር የሃብት ጭማሪ ማስመዝገባቸውን የጠቆመው ፎርብስ፤ በአንድ አመት ውስጥ ይህን ያህል የሃብት ጭማሪ በማስመዝገብ በታሪክ የመጀመሪያው የአለማችን ባለጠጋ መሆናቸውን አመልክቷል፡፡
ባለፉት 24 አመታት ውስጥ ለ18 ጊዜያት የአለማችን ቁጥር አንድ ባለጸጋ ሆነው የዘለቁት የማይክሮሶፍቱ መስራች አሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስ ዘንድሮ 90 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት ይዘው ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ያሉ ሲሆን የታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ መስራች ማርክ ዙክበርግ በ71 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት አምስተኛው የአለማችን ቢሊየነር ሆኗል፡፡
የአመቱ የተጣራ ሃብታቸው 3.1 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ የተነገረላቸው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አምና ከነበሩበት የሃብት ደረጃ በ222 ደረጃዎች ዝቅ ብለው 766ኛ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
አለማችን ዘንድሮ ከመቼውም በላይ በርካታ ቢሊየነሮችን ማፍራቷን የጠቆመው ፎርብስ፤አምና 2 ሺህ 43 የነበረው የቢሊየነሮች ቁጥር ዘንድሮ ወደ 2 ሺህ 208 ከፍ ማለቱንና የአለማችን ቢሊየነሮች ጠቅላላ ሃብት ድምር አምና ከነበረበት የ7.7 ትሪሊዮን ዶላር ጭማሪ በማድረግ ዘንድሮ 9.1 ትሪሊዮን ዶላር መድረሱን ገልጧል፡፡
ከሙስና ጋር በተያያዘ ባለሃብቶቿን ስታስር የከረመቺውን የሳኡዲ አረቢያ ባለሃብቶች በዘንድሮው የባለጠጎች መዝገብ ውስጥ አለማካተቱን ያስታወቀው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፤ ባለፈው አመት በዝርዝሩ ውስጥ ተካትተው የነበሩ 10 የሳኡዲ ቢሊየነሮችን ስም ከዝርዝሩ መፋቁን አመልክቷል፡፡
ከሳኡዲ የሙስና ጉዳይ ጋር በተያያዘ ከፎርብስ ዝርዝር ውስጥ ከተፋቁት ባለጠጎች መካከል አምና 18.7 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት የነበራቸው ልኡል አልዋሊድ ቢን ታላል እና 8.1 ቢሊዮን ዶላር የነበራቸው ሼክ ሙሀመድ ሁሴን አል አሙዲን ይገኙበታል፡፡

 

Read 6652 times