ለረጅም ዓመታት ልደታቸውን በብሄራዊ በዓልነት እጅግ በደመቀ ሁኔታ ከህዝባቸው ጋር በአደባባይ ሲያከብሩ የኖሩት የቀድሞው የዚምባቡዌ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤ ባለፈው ረቡዕም የ94ኛ አመት ልደታቸውን ከወትሮው በፈዘዘ መልኩ እንደነገሩ አክብረዋል፡፡
ሙጋቤ ምንም አንኳን ስልጣን ከለቀቁ ወራትን ቢያስቆጥሩም፣ የልደት በዓላቸው ግን የዚምባቡዌ ወጣቶች ቀን በሚል ስያሜ በብሄራዊ ደረጃ ወጣቶችን ለበጎ ስራ በማሰማራት መከበሩን የዘገበው ኒውስ 24፤ እንደ ወትሮው በኬክና በሻምፓኝ፣ በክምር ስጦታና በደማቅ ሙዚቃ፣ በይፋ በአደባባይ አለመከበሩን አመልክቷል፡፡
የሙጋቤ ልደት በየአመቱ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠር በጀት ተመድቦለት በሚገርም ፈንጠዝያና በግዙፍ ኬክ ይከበር እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ፓርቲያቸው ዛኑ ፒኤፍ ግን ከቀናት በፊት ባወጣው መግለጫ የሙጋቤ ልደት ያለ ብዙ ወጪ ቀለል ብሎ እንደሚከበር ማስታወቁን ገልጧል፡፡