Saturday, 17 February 2018 15:01

ቻይና ከ60 ሺህ በላይ ወታደሮችን ለዛፍ ተከላ ልትቀጥር ነው

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የደን ሽፋንን በተፋጠነ የዛፍ ተከላ በማሳደግ፣ የአየር ብክለትን ለመዋጋት ቆርጦ የተነሳው የቻይና መንግስት፤ ከስራ ገበታቸው ተሰናብተው የነበሩ 60 ሺህ ወታደሮችን መልሶ በመቅጠር በችግኝ ተከላ ስራ ላይ ሊያሰማራ ማቀዱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ከዚህ በፊት በመደበኛ ውትድርና ሙያ ላይ ያገለግሉ የነበሩና ከስራ ገበታቸው የተሰናበቱት እነዚህ ወታደሮች፤ የቻይና መንግስት በአገሪቱ የተለያዩ ግዛቶች ሊያከናውናቸው ባቀዳቸው ሰፋፊ የደን ልማት ፕሮጀክቶች ውስጥ በችግን ተከላ ስራ ላይ እንደሚሰማሩ የጠቆመው ዘገባው፤በተለይም የኢንዱስትሪ ጭሶችን በብዛት በማውጣት ከፍተኛ የአየር ብክለትን በሚያስከትሉ አካባቢዎች ብዛት ያላቸው ዛፎችን ለመትከል መታቀዱን አመልክቷል።
ቻይና በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ብቻ 84 ስኩየር ኪሎ ሜትር በሚሸፍን ቦታ ላይ በርካታ ዛፎችን የመትከል እቅድ ይዛ በስፋት እየተንቀሳቀሰች እንደምትገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ በደን ይሸፈናል ተብሎ የታቀደው ቦታ ስፋት ከአየርላንድ አጠቃላይ የቆዳ ስፋት ጋር ተመጣጣኝ መሆኑን አስረድቷል።
 አገሪቱ የደን ሽፋኗን አሁን ከሚገኝበት 21 በመቶ፣ በመጪዎቹ ሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ ወደ 23 በመቶ ከፍ ለማድረግ ማቀዷንና የደን ሽፋኑ እ.ኤ.አ እስከ 2035 ድረስ 26 በመቶ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አመልክቷል፡፡

Read 1138 times