Saturday, 17 February 2018 14:55

“እስኪ ልየው” የሙዚቃ አልበም ተመረቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ የሽፋን ፎቶ በ400 ሺህ ብር ተሽጧል

    በቅርቡ በገበያ ላይ የዋለው “እስኪ ልየው” የተሰኘው የድምጻዊት ሄለን በርሄ የሙዚቃ አልበም ባለፈው ሳምንት አርብ ምሽት በማማስ ኪችን በተከናወነ ልዩ ፕሮግራም የተመረቀ ሲሆን፣ በእለቱ በይፋ ተመርቆ ለእይታ የበቃውና በአልበሙ ውስጥ ከተካተቱት 14 ሙዚቃዎች አንዱ የሆነው የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ ፎቶ ግራፍ ለጨረታ ቀርቦ በ400 ሺህ ብር ተሽጧል፡፡
ኡቡንቱ አርት ማኔጅመንት እና ንጉስ ኢንተርቴንመንት በጋራ ያዘጋጁትና የካቲት 2 ቀን 2010 ዓ.ም ምሽት ወሎ ሰፈር በሚገኘው ማማስ ኪችን በተከናወነው የአልበሙ የምረቃ ፕሮግራም ላይ በርካታ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የድምጻዊቷ አድናቂዎችና ተጋባዥ እንግዶች የታደሙ ሲሆን፣ ድምጻዊቷ አዳዲስና ቆየት ያሉ ተወዳጅ ሙዚቃዎቿን በአስገራሚ ብቃት በማቀንቀን ታዳሚውን ስታዝናና አምሽታለች፡፡
ድምጻዊት ሄለን በርሄ፣ በአዲሱ አልበም ውስጥ የተካተተውን የኔ ቆንጆ የተሰኘ ተወዳጅ ዜማ ያበረከቱላትን ታዋቂውን የዜማ ደራሲና የማንዶሊን ተጫዋች አቶ አየለ ማሞን ጨምሮ ለአልበሙም ሆነ ለሙዚቃ ክሊፑ ስኬታማነት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ባለሙያዎችን በተደጋጋሚ ስታመሰግን አምሽታለች፡፡
ምነው ሸዋ ኢንተርቴንመንት ፕሮዲዩስ ያደረገውና 350 ሺህ ብር ያህል ወጪ እንደተደረገበት የተነገረለት እንዲሁም ከ50 በላይ ተዋንያን የተሳተፉበት “ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ በምሽቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለእይታ በበቃበት ቅጽበት፣ በዩቲዩብ ድረገጽ የተለቀቀ ሲሆን፣ የፕሮግራሙ ታዳሚያን አድናቆታቸውን በሚገርም ሁኔታ ሲገልጹ ተስተውለዋል፤ በዩቲዩብም ብዙ ተመልካቾች እያዩት እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ የሽፋን ፎቶ ግራፍ በምሽቱ ለጨረታ የቀረበ ሲሆን፣ የድምጻዊቷ አድናቂዎችና በዝግጅቱ ላይ የታደሙ የሙዚቃ አፍቃሪያን ፎቶግራፉን በእጃቸው ለማስገባት ረጅም ፉክክር ካደረጉ በኋላ፣ በስተመጨረሻም 400 ሺህ ብር ያቀረቡት የማማስ ኪችን ባለቤት ጨረታውን አሸንፈዋል፡፡
በአልበሙ የምረቃ ስነስርዓት ላይ ጸደኒያ ገብረ ማርቆስ፣ ጌትሽ ማሞ፣ ዳግማዊት ጸሃዬና አስገኘው አሽኮ (ዴንዳሾ)ን ጨምሮ ሌሎች ተጋባዥ ድምጻውያን የሙዚቃ ስራዎቻቸውን ለታዳሚያን አቅርበዋል፡፡

Read 3453 times