Sunday, 11 February 2018 00:00

ዶ/ር መረራ ወደ መደበኛ የፓርቲ ሥራቸው ተመለሱ

Written by 
Rate this item
(4 votes)

  ከእንግሊዝ አምባሳደር ጋር በእስረኞችና በሀገሪቱ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ተወያይተዋል

    በቅርቡ ከእስር የተለቀቁት ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ወደ መደበኛ የፓርቲ ሥራቸው ለመመለስ መወሰናቸውን የገለጹ ሲሆን በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ከሆኑት ሱዛን ሞርሄድ ጋር መወያየታቸውም ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ ባወጣው መረጃ፤ አምባሳደሯ በወቅቱ የሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ከዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር መወያየታቸውን ጠቁሟል። ውይይቱን በተመለከተ ለአዲስ አድማስ ያብራሩት ዶ/ር መረራ፤ ስለ ማረሚያ ቤቶች የእስረኞች አያያዝ፣ ስለ ወቅቱ የሀገሪቱ ሁኔታና ወደፊት ሊሆን ስለሚገባው ጉዳይ ከአምባሳደሯ ጋር በስፋት መነጋገራቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይ ህብረተሰቡ በመንግስት ላይ ያለውን ተቃውሞ የሰው ህይወት መቅጠፍን የሚያስከትል ግጭት ሳይፈጠር፣ በሰላማዊ መንገድ በሚያሰማበት ሁኔታ ላይ በትኩረት ተወያይተናል ብለዋል - ዶ/ር መረራ።
በተመሳሳይ ከሁለት ሳምንት በፊት በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ከሆኑት አምባሳደር ቫግ ነር ጋር መወያየታቸውን  መዘገባችን  ይታወሳል፡፡
ከእስር በተለቀቁ ወቅት በፖለቲካ ትግላቸው ይቀጥሉ እንደሆነ አለመወሰናቸውን የተናገሩት ዶ/ር መረራ፤ በአሁኑ ወቅት በኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) የሊቀ መንበርነት ሥራቸው ለመቀጠል መወሰናቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ከአደአ በርጋ ህዝብ በቀረበላቸው ጥሪ መሰረት፣ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ወደ አካባቢው በተጓዙበት ወቅት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ከፍተኛ የአድናቆት አቀባበል እንዳደረጉላቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡   
በተመሳሳይ ዶ/ር መረራ፣ ከሁለት ሳምንት በፊት በአምቦ ከተማ፣ተቀራራቢ ቁጥር ያለው ህዝብ ደማቅ   አቀባበል እንዳደረገላቸው ይታወቃል፡፡

Read 5868 times