Sunday, 11 February 2018 00:00

ኢትዮጵያዊው በተመድ የስነ-ህዝብ ፈንድ ም/ ዋና ዳይሬክተርነት ተሾሙ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   *ዋና ዳይሬክተሯን ተክተው ይሰራሉ ተብሏል

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ፣ በአለማቀፍ ተቋማት የረጀም አመታት የከፍተኛ አመራርነት ልምድ ያላቸውን ኢትዮጵያዊውን አቶ ደረጀ ወርዶፋን የተመድ የስነ-ህዝብ ፈንድ የፕሮግራም ምክትል ዋና ዳይሬክተር አድርገው መሾማቸውን ከትናንት በስቲያ አስታውቀዋል፡፡ ኢትዮጵያዊው፤በቅርቡ የስነ-ህዝብ ፈንድ ዋና ዳይሬክተር ሆነው የተሾሙትን የፓናማ ተወላጇን ናታንያ ካኔም ተክተው እንደሚሰሩም ነው የተገለጸው፡፡
በተለያዩ አለማቀፍና አህጉራዊ ተቋማት ውስጥ በከፍተኛ የስራ ሃላፊነቶች ላይ ከ28 አመታት በላይ የዘለቀ ስኬታማ አመራር በመስጠት የካበተ ልምድ ያላቸው ኢትዮጵያዊው አቶ ደረጀ፣ በተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ሆነው በማገልገል ላይ ያሉትን ናታሊያ ካኔምን እንደሚተኩ ተመድ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በአለማቀፉ ኤስኦኤስ የህጻናት መንደር፣ የምስራቃዊና ደቡባዊ አፍሪካ አለማቀፍ ክልላዊ ዳይሬክተር የሆኑትና 4 ሺህ 500 ያህል ሰራተኞችን በስራቸው በማስተዳደር ላይ የሚገኙት አቶ ደረጀ፣ ብቃት ባለው አመራር በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ፈተናዎችን በመቋቋም፣ በአብዛኛው አፍሪካን ተደራሽ ያደረጉ በርካታ ስራዎችን በስኬታማነት እንዳከናወኑ መግለጫው አስረድቷል፡፡
አቶ ደረጀ ከዚህ ቀደምም አሜሪካን ፍሬንድስ ሰርቪስ ኮሚቴ በተባለው ተቋም በክልላዊ ዳይሬክተርነት፣ በኡጋንዳ የኦክስፋም ሃላፊ፣ በሴቭ ዘ ችልድረን በምክትል የፕሮግራም ዳይሬክተርነትና በሌሎች ታላላቅ ተቋማት በከፍተኛ የስራ ሃላፊነቶች ላይ በማገልገል ብቃታቸውን ማስመስከራቸውን አስታውሷል፡፡
ኢትዮጵያዊው አቶ ደረጀ ከኦክስፎርድ ብሩከስ ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን በማስተርስ፣ በለንደን ስኩል ኦፍ ኢኮኖሚክስ በሶሻል ፖሊሲ ኢን ዲቨሎፒንግ ካንትሪስ በማስተርስ መመረቃቸውንና፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውንም በቢዝነስ ማኔጅመንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማግኘታቸውን መግለጫው አክሎ ገልጧል፡፡  

Read 2342 times