Monday, 05 February 2018 00:00

ናሚቢያ ባለስልጣናት ወደ ውጭ አገራት እንዳይጓዙ ከለከለች

Written by 
Rate this item
(3 votes)

ስራ ፈትተው ከሚቀለቡ 6 ሺህ ወታደሮች፣ የተወሰኑት በግድ እረፍት ይወጣሉ

   ፕሬዚዳንቱ ወጪን ለመቀነስ ሲሉ ለሰሞኑ የህብረቱ ስብሰባ፣ የግል አውሮፕላናቸውን ትተው፣ በመደበኛ አውሮፕላን ነበር የመጡት
ከፍተኛ የፋይናንስ እጥረት የገጠመው የናሚቢያ መንግስት፤ወጪን ለመቆጠብ በሚል ሚኒስትሮችን፣ ምክትል ሚኒስትሮችንና ከፍተኛ የመንግስት ተቋማት ሃላፊዎችን ጨምሮ ሁሉም የአገሪቱ ባለስልጣናት ወደ ውጭ አገራት እንዳይሄዱ መከልከሉን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
ማንኛውም የአገሪቱ ባለስልጣን ለስብሰባ፣ ለስልጠናና ለሌሎች ጉዳዮች ከአገሪቱ ውጭ የሚያስወጣው ጉዞ ካለ በአፋጣኝ እንዲሰርዝ መንግስት መመሪያ ማስተላለፉን የጠቆመው ዘገባው፤ የጉዞ ክልከላው ቢያንስ እስከ ወሩ መጨረሻ ተግባራዊ ሆኖ እንደሚቆይና ይራዘማል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል፡፡ በውጭ አገራት ጉዞ ሳቢያ ለባለስልጣናት ከፍተኛ ወጪ ማውጣት እንዲቆም ያሳሰቡት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሀጌ ጌንቦ፤ በሰሞኑ የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ ወደ አዲስ አበባ በመጡበት ወቅትም የግል አውሮፕላናቸውን ትተው፣ የህዝብ ማመላለሻ መደበኛ አውሮፕላን መጠቀማቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የናሚቢያ ኢኮኖሚ በአብዛኛው በማዕድን ኤክስፖርት ገቢ ላይ የተመሰረተ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የአለም አቀፍ ገበያ መቀዛቀዝ ኢኮኖሚዋን ክፉኛ እንደጎዳውና የፋይናንስ እጥረት የገጠመው የአገሪቱ መንግስት መሰል ወጪዎችን ለመቀነስ እርምጃ መውሰድ መጀመሩን አስረድቷል።
ስራ ፈትተው በጦር ካፕሞች ለሚኖሩ የጦር ሃይሉ አባላት ደመወዝ በአግባቡ መክፈልም ሆነ የእለት ምግብና ውሃን ጨምሮ የተለያየ ወጫቸውን መሸፈን ያቃተው የአገሪቱ መንግስት፣ ከሰሞኑ በሺህዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቹን የአመት እረፍት ለማስወጣትና በእረፍት ላይ ለሚገኙትም ተመልሰው እንዳይመጡ መመሪያ ለመስጠት መወሰኑን ዘ ናሚቢያን የተባለው የአገሪቱ የግል ጋዜጣ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መከላከያ ሚ/ር ለ2018 የበጀት አመት 5.6 ቢሊዮን የአገሪቱ ዶላር እንደተመደበለት ያስታወሰው ዘገባው፣ አገሪቱ 15 ሺህ ያህል ወታደሮች እንዳሏትና 6 ሺህ ያህሉ ስራ ፈትተው በጦር ካምፖች ውስጥ እንደሚኖሩ መነገሩንም አክሎ ገልጧል፡፡

Read 4433 times