Monday, 05 February 2018 00:00

ፌስቡክ በ3 ወራት 4.3 ቢሊዮን ዶላር አትርፏል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  በየቀኑ 50 ሚሊዮን ሰዓታት ፌስቡክ ላይ ይጠፋሉ

    ታዋቂው የማህበራዊ ድረ-ገጽ ፌስቡክ፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017፣ የመጨረሻው ሩብ አመት፣ ሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ የ4.3 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ ማግኘቱንና ይህም ካለፈው የሩብ አመት ትርፍ፣ በ61 በመቶ ብልጫ እንዳለው ኩባንያው ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የኩባንያውን መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ማርክ ዙክበርግን ጠቅሶ ዘ ኢንዲፔንደንት እንደዘገበው፤ ፌስቡክ በተጠቀሰው የሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ በድምሩ 12.7 ቢሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን፣ የወርሃዊ ተጠቃሚዎቹ ቁጥርም 2.13 ቢሊዮን ያህል ደርሷል። ፌስቡክን በሞባይል የሚጠቀሙ ደንበኞች ቁጥር ማደጉ በሩብ ዓመቱ ከፍተኛ ትርፍ እንዲያገኝ አስችሎታል ያለው ዘገባው፤ በየዕለቱ ፌስቡክን የሚጠቀሙ ደንበኞች ቁጥርም 1.4 ቢሊዮን መድረሱን አስረድቷል፡፡
ፌስቡክ የተጠቃሚዎቹን ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ እየተሻማና ስራ እያስፈታ ነው በሚል የሚሰነዘርበትን ትችት በማጤን፣ በሩብ አመቱ ተጠቃሚዎች በየቀኑ ፌስቡክ ላይ የሚያጠፉትን ጊዜ በተወሰነ መልኩ ለመቀነስ የሚያስችል እርምጃ መውሰዱን የጠቆመው ዘገባው፤ በአንድ ቀን ውስጥ ተጠቃሚዎች በፌስቡክ ላይ የሚያጠፉትን አጠቃላይ ድምር ጊዜ ወደ 50 ሚሊዮን ሰዓታት ዝቅ ማድረጉን አስታውሷል፡፡
በአዲሱ የፈረንጆች አመት የዓለማችን የዲጂታል ማስታወቂያ ገበያ ውስጥ 266 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ይንቀሳቀሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ በዚህ ገበያ ውስጥ ፌስቡክ 18.4 በመቶ ያህል ድርሻ ይኖረዋል ተብሎ እንደሚገመት አመልክቷል፡፡

Read 1463 times