Sunday, 27 August 2017 00:00

“መኢአድ” እና “ሰማያዊ” ለአዲስ አበባ ምርጫ ተዋህደው ሊወዳደሩ ነው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(7 votes)

“በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ፣ 195 አመራርና አባሎቻችን ታስረዋል”
    ሰማያዊ ፓርቲና መኢአድ ሰሞኑን ከተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች ጋር ባደረጉት ውይይት፣ በቀጣይ ዓመት ለሚካሄደው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምርጫ፣ተዋህደው ለመወዳደር ማቀዳቸውን አስታውቀዋል፡፡ የፓርቲዎቹ አመራሮች፣ ከ20 በላይ ከሚሆኑ ዲፕሎማቶች ጋር በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁና አፈፃፀሙ፣ በቀጣይ የፓርቲዎቹ የጋራ እቅድና በአዲስ አበባ ከተማ የ2010 ምርጫ ዝግጅት ላይ እንዲሁም በፖለቲካ ምህዳር መጥበብ ዙሪያ ውይይት ማካሄዳቸውን  ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡   
ሁለቱ ፓርቲዎች በአሁን ወቅት ለአባሎቻቸው በጋራ የአቅም ግንባታ ስልጠና እየሰጡ መሆኑን የገለፁት አመራሮቹ፣ በክልል፣ በዞንና በወረዳ ያላቸውን ተናጥላዊ አደረጃጀት ወደ አንድ ለማምጣት እየተጉ እንደሆነ ጠቁመው፣ በቀጣዩ ዓመት በሚደረገው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምርጫ አንድ ውህድ ፓርቲ ሆነው ለመወዳደር ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡ ከሁለቱም ፓርቲዎች ሰዎች ተወክለው፤ የፓርቲዎቹን የውህደት ሂደት በማፋጠን ላይ እንደሚገኙም አስታውቀዋል፡፡  
ሁለቱ ፓርቲዎች ተዋህደው በቀጣዩ ምርጫ፣ እንደ አንድ ፓርቲ፣ ጠንካራ ተገዳዳሪ ሆነው ለመቅረብ በዝግጅት ላይ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ሠላማዊ የመንግስት ሽግግር ለማድረግ የተቻላቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉም ለዲፕሎማቶቹ ማስረዳታቸውን ገልጸዋል፡፡ ሌሎች ተመሣሣይ አላማ ያላቸውን ፓርቲዎች ወደ ውህደቱ በማምጣትም፣ ለቀጣዩ ሃገር አቀፍ ምርጫ፣ አንድ ጠንካራ ፓርቲ የመመስረት ውጥን እንዳላቸው አስታውቀዋል - ፓርቲዎቹ፡፡
በአሁን ወቅት የፖለቲካ ምህዳሩ መዘጋቱን የጠቆሙት የፓርቲዎቹ አመራሮች፤ በህገ መንግስቱ የተደነገገው ህዝባዊ ስብሰባዎችን የማድረግ መብትም እንደተነፈገ ገልጸዋል፡፡ ህዝባዊ ስብሰባ እንዳያደርጉ መከልከላቸው ደግሞ ከህዝብ ጋር ተገናኝተው፣ በሠብአዊ መብት አያያዝ፤ በፌዴራል ሥርአቱ፣ በመሬት ስሪትና  በውጭ ጉዳይ ፖሊሲ እንዲሁም በነፃ ገበያና ሌሎች አገራዊ አጀንዳዎች ዙሪያ ለመወያየት የያዙትን እቅድ እንዳከሸፈባቸው  ጠቁመዋል፡፡   
በሌላ በኩል፣ ለ11 ወራት ያህል የዘለቀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ፣ 121 የሠማያዊና 74 የመኢአድ አመራሮችና አባላት ለእስር መዳረጋቸውን ከዲፕሎማቶቹ ጋር ባደረጉት ውይይት ማንሳታቸውን ገልጸዋል፡፡  
“አባሎቻችን ታስረውብናል፣ ከቤት ንብረታቸውም እንዲፈናቀሉ ተደርገውብናል” ያሉት ፓርቲዎቹ፤ በተለይ በደሴ፣ ደብረ ማርቆስ፣ ባህር ዳር፣ ጎንደር፣ ምዕራብ ጉጂ - ገላና እና ጌዴኦ ዞን  የሚገኙ አባላት ወህኒ እንደወረዱ ተናግረዋል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በቆየባቸው 11 ወራቶች ውስጥ በፓርቲ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው ላይ የደረሱ ወከባዎች የሚያደርጉትን ሰላማዊ ትግል እንዳዳከመባቸው ጠቁመው፣ አብዛኛው መዋቅራቸውና ቢሮዎቻቸውም እንደተዘጉባቸው አስታውቀዋል - የፓርቲዎቹ አመራሮች፡፡

Read 3045 times