Sunday, 06 August 2017 00:00

ባህር ዛፍን ከእንጦጦ ተራራ ለማስወገድ፣ 130 ሺ ሀገር በቀል ችግኞች ይተከላሉ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)


     የባህር ዛፍ ተክልን ከእንጦጦ ተራራ ላይ በማስወገድ በሀገር በቀል ዛፎች ለመተካት እስከ 2012 ዓ.ም የሚቆይ እቅድ የተያዘ ሲሆን ዘንድሮም ከ130 ሺህ በላይ የሀገር በቀል ዛፍ ችግኞች ይተካላሉ ተብሏል፡፡
ከዚሁ ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ የኢትዮ ቴሌኮም እና የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ዜድቲኢ ሰራተኞች ከትናንት በስቲያ በተራራው ላይ 200 ያህል ሀገር በቀል ዛፎችን የተከሉ ሲሆን ይህን ተግባርም ላለፉት 4 ዓመታት ሲተገብሩት እንደቆዩ ተገልጿል፡፡ በ4 ዓመታት ከተከሉት መካከል 80 በመቶው መፅደቁም ተገልጿል፡፡
የእንጦጦ ተራራ በአብዛኛው በባህር ዛፍ ተክል ተሸፍኖ እንደነበር ለአዲስ አድማስ ያስረዱት የጉለሌ ክፍለ ከተማ የብዝሃ ህይወት ጥበቃ ባለሙያ አቶ ደጀኔ ሙሉጌታ፤ ከ9 ዓመት በፊት ይፋ በተደረገው ባህር ዛፍን በሀገር በቀል የመተካት እቅድ አብዛኛው የተራራው ክፍል ከባህር ዛፍ ነፃ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ እስከ 2012 ዓ.ም ሙሉ ለሙሉ ተራራውን ከባህር ዛፍ ነፃ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የባህር ዛፍ ቅጠር ሲረግፍ በቶሎ ወደ አፈርነት የመቀየር ባህሪ የሌለው በመሆኑ፣ በብዝሃ ህይወት ላይ ጉዳት እንደሚያስከትል በመረጋገጡ ነው እንዲወገድ የተፈለገው ተብሏል፡፡ በተራራው ላይ የተለያዩ ተቋማት ሀገር በቀል ችግኞችን የሚተክሉት ይሄን ዓላማ ለማሳካት ሲሆን ከተቋማቱ ውስጥም ዜድቲኢ ተጠቃሽ መሆኑን አቶ ደጀኔ ተናግረዋል፡፡

Read 2529 times