Sunday, 09 July 2017 00:00

የ40/60 ቤት እድለኞች በወር ውስጥ ቤታቸውን ይረከባሉ ተብሏል

Written by 
Rate this item
(16 votes)

     መንግስት በአጠቃላይ ከ725 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ በማድረግ ሰርቻቸዋለሁ ያላቸው 972 የ40/60 መኖሪያ ቤቶች  እጣ ዛሬ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ የሚወጣ ሲሆን ዕድለኞች በወር ውስጥ ቤታቸውን ይረከባሉ ተብሏል፡፡  
ዛሬ ለእጣ ከተዘጋጁት 972 ቤቶች የሚጠበቅባቸውን የቤት ዋጋ ሙሉ ለሙሉ የከፈሉ 11 ሺህ 88 ቤት ፈላጊዎች የሚወዳደሩ ሲሆን ከነዚህ እድለኞች ውስጥ 20 በመቶ ለመንግስት ሰራተኞች፣ 3 በመቶ (29 ቤቶች) ለዳያስፖራዎች ቅድሚያ እድል የሚሰጥባቸው ይሆናሉ፡፡
የቤቶቹን እጣ አወጣጥ አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ የከተማ አስተዳደሩ፣ የኮንስትራክሽን ሚኒስቴርና ቤቶች ልማት ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን ለእነዚህ ግንባታቸው ከተጀመረ ከ4 ዓመት በኋላ ለተጠናቀቁ 972 ቤቶች አጠቃላይ ወጪ፣ ቤት ፈላጊዎች ከቆጠቡት በተጨማሪ መንግስት ከ725 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ አድርጎባቸዋል ተብሏል፡፡
የ40/60 የቤት ፕሮግራም ከ4 ዓመት በፊት 44 ሲደረግ ባለ 1 መኝታ ቤት 55 ካሬ ሜትር፣ ባለ 2 መኝታ 75 ካ.ሜ እንዲሁም ባለ 3 መኝታ 100 ካ.ሜትር ስፋት እንዲኖራቸው ታቅዶ የነበረ ቢሆንም ኋላ ላይ በተደረገ የዲዛይን ማሻሻያ ባለ 1 መኝታ ቤት እንዳይኖር ተደርጎ፣ ባለ 1 የነበረው ወደ ባለ 2 መኝታ ቤት 125 ካ.ሜትር ስፋት፣ ባለ 2 የነበረው ወደ ባለ 3 መኝታ ከፍ ተደርጎ፣ በ150 ካ.ሜትር ላይ እንዲሁም ባለ 3 የነበረው ወደ ባለ 4 መኝታ ቤት ከፍ ተደርጎ፣ 168 ካ.ሜትር ስፋት እንዲኖራቸው መደረጉ ተገልጿል፡፡  
የቤቶቹ ዋጋም ቀደም ሲል በካሬ ሜትር በ3200 ብር ታስቦ የነበረው ወደ 5680 ብር ከፍ ማለቱን፣ መንግስት በእያንዳንዱ ካሬ ሜትር ላይ የ720 ብር ድጎማ አድርጎ፣ እድለኞች ቤቱን በካሬ ሜትር 4918 ብር ሂሳብ እንዲረከቡ ማመቻቸቱን በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም መሰረት፤ ዛሬ እጣ የሚወጣባቸው መኖሪያ ቤቶች ላይ እያንዳንዱ ባለ እድለኛ ቀድሞ ከነበረው ዋጋ ላይ በካሬ ሜትር 1718 ብር ጭማሪ እንደሚከፍል ታውቋል፡፡
በቤቶቹ ዋጋ ላይ በጠቅላላው 170 ሚሊዮን ብር ድጎማ መደረጉን እንዲሁም አስተዳደሩ ፓርኪንግ ለመሳሰሉ ወጪዎች 140 ሚሊዮን፣ ለእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያ 97 ሚሊዮን እና ለቫት 168 ሚሊዮን የከፈለውን ጨምሮ 725 ሚሊዮን ብር ድጎማ ማድረጉ ተመልክቷል፡፡
ለመኖሪያ ቤትነት እጣ ከሚወጣባቸው ቤቶች በተጨማሪ 320 የንግድ ቤቶችም በእለቱ በመነሻ ዋጋ በካሬ ሜትር 172 ሺህ ብር ለጨረታ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ ከ40/60 ቤቶች የተወሰኑት ለመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ እንዲሰጥ ጥያቄ መቅረቡን የጠቆሙት የአስተዳደሩ ም/ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታው፤ዕድለኞች ክፍያ ፈፅሞ ቤቶቹን ለመውሰድ የሚከብዳቸው ከሆነ መንግስት ራሱ ቤቱን ይገዛዋል፤ዋጋው አሁን በዝቶብኛል ያሉ በቀጣይ በሚወጡ እጣዎች የመካተት እድል ይኖራቸዋል ብለዋል፡፡  
የንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ በቃሉ ዘለቀ በበኩላቸው፤ ዛሬ እጣ የሚወጣባቸው የክራውንና የሠንጋ ተራ ሳይት ቤቶች መሠረተ ልማት እንደተሟላላቸውና በጥራት መሰራታቸውን ሙሉ ለሙ አረጋግጦ ባንኩ መረከቡን አስታውቀዋል፡፡
በአጠቃላይ በ40/60 የቤቶች ፕሮግራም በ2005 ዓ.ም 164 ሺህ ያህል ቤት ፈላጊዎች ተመዝግበው የነበረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት 140 ሺህ ቤት ፈላጊዎች ቁጠባቸውን ሳያቋርጡ አድላቸውን እየተጠባበቁ ነው ተብሏል፡፡ በቀጣይ ዓመትም 20 ሺህ ቤቶችን ለተመዝጋቢዎች ለማስተላለፍ እቅድ መያዙን የስራ ሃላፊዎቹ አብራርተዋል፡፡

Read 9356 times