Sunday, 02 July 2017 00:00

ዋልያዎቹን በአህጉራዊ ደረጃ በቂ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በአህጉራዊ ደረጃ ለሚደረጉ ውድድሮች በሚኖረው  የማጣርያ ግጥሚያዎች ተሳትፎ  በቂ ትኩረት ያስፈልገዋል፡፡ በ2019 የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ከሁለት ሳምንት በፊት በአክራ ከተማ 5ለ0 ከባድ ሽንፈት የገጠማቸው ዋልያዎቹ ይህ ደካማ አጀማመራቸው ብዙዎችን አላስደሰተም፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ወደ አፍሪካ ዋንጫው የምድብ ማጣርያ የሚመለሰው ከ8 ወራት በኋላ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
በሌላ በኩል በ2018 እ.ኤ.አ ኬንያ ለምታዘጋጀው 5ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ቻን 2ኛ ዙር ማጣርያ ሰሞኑን ዝግጅታቸውን የሚቀጥሉ ይሆናል፡፡ በቻን 2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመሪያው ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከሜዳ ውጭ የሚገናኘው ከጅቡቲ አቻው ጋር ነው፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና  አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ በቻን  ከጅቡቲ ጋር ከሜዳ ውጭ ለሚገናኙበት  የ2ኛ ዙር ማጣርያ ጨዋታ  ዝግጅት   አዳዲስ ተጫዋቾችን ጠርተዋል፡፡ ዋና አሰልጣኙ በአገር ውስጥ የሊግ ተጨዋቾች የተደራጀ ስብስባቸውን ይዘው  ለዝግጅት   ወደ ድሬዳዋ እንደሚያመሩ ይጠበቃል፡፡በ2018 እ.ኤ.አ ኬንያ ለምታስተናግደው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ ኮታ ለ3 አገራት ነው። ኬንያ በአዘጋጅነቷ በቀጥታ ማለፋን ያረጋገጠች ሲሆን ሌሎች 2 ብሔራዊ ቡድኖች በ2ኛ እና 3ኛ ዙር በሚካሄድ ቅድመ ማጣሪያዎች የሚወሰኑ ይሆናል፡፡ ከ2 ሳምንታት በኋላ በሚቀጥለው የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ደቡብ ሱዳን ከኡጋንዳ፤ ጅቡቲ ከኢትዮጵያ፣ ታንዛኒያ ከሩዋንዳ እንዲሁም ብሩንዲ ከሱዳን ይገናኛሉ፡፡
ለቻን 2018 ማጣርያ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የተጫዋቾች ዝርዝር
ግብ ጠባቂዎች
ጀማል ጣሰው (ጅማ አባ ቡና)፣ ሳምሶን አሰፋ (ድሬዳዋ ከተማ) ፣ ለአለም ብርሃኑ (ሲዳማ ቡና)
ተከላካዮች
አስቻለው ታመነ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ ሳላዲን በርጌቾ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)፣ አብዱልከሪም መሃመድ (ኢትዮጵያ ቡና)፣ አንተነህ ተስፋዬ (ሲዳማ ቡና)፣ ሙጂብ ቃሲም (አዳማ ከተማ)፣ ስዩም ተስፋዬ (ደደቢት) ፣ ደስታ ዮሀንስ (ሀዋሳ ከተማ)፣ አምሳሉ ጥላሁን (ፋሲል ከተማ)
አማካዮች
ሽመክት ጉግሳ (ደደቢት)፣ ሙሉአለም መስፍን (ሲዳማ ቡና)፣ ጋዲሳ መብራቴ (ሃዋሳ ከተማ) ፣ ታፈሰ ሰለሞን (ሀዋሳ ከተማ) ፣ ምንተስኖት አዳነ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ ናትናኤል ዘለቀ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ በኃይሉ አሰፋ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)
አጥቂዎች
ጌታነህ ከበደ (ደደቢት)፣ አዲስ ግደይ (ሲዳማ ቡና)፣ አብዱልራህማን ሙባረክ (ፋሲል ከተማ)፣ ሳላዲን ሰዒድ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)
በ2019 እኤአ ላይ ካሜሮን ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ  በተጀመረው የምድብ ማጣርያ በምድብ 6 ጋና በአክራ ኢትዮጵያን 5ለ0 ስታሸንፍ ሴራሊዮን በሜዳዋ ኬንያን 2ለ1 ረታለች፡፡
ሴራሊዮን በዋና ከተማዋ ፍሪታውን በሚገኘው ብሄራዊ ስታድዬም ኬንያን 2ለ1 ስታሸንፍ ዋሌይ በ22ኛው ደቂቃ ላይ እንዲሁም አምበሉ ባንጉራ በ69ኛው ደቂቃ ላይ በፍፁም ቅጣት ምት ባስቆጠሯቸው ጎሎች ነው፡፡ የኬንያን ብቸኛ ግብ ያስቆጠረው ኦሉንጋ በ75ኛው ደቂቃ ላይ ነበር፡፡ ሴራሊዮን ኬንያን በሜዳዋ በማሸነፍ ያሳየችው ጅማሮ ለብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ከፍተኛ መነቃቃት ፈጥሮላቸዋል፡፡ ሎን ስታርስ የሚባለው ብሄራዊ ቡድኑን በአምበልነት የሚመራው ባንጉራ ለቢቢሲ በሰጠው አስተያየት ለማንም የማንመለስ ጠንካራ ቡድን ነን ሲል ተናግሯል፡፡ ሴራሊዮን በአፍሪካ ዋንጫ ለ2 ጊዜያት የተሳተፈችው በ1994 እና 1996 እኤአ ላይ ነበር፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ309 ነጥብ 113ኛ ላይ ትገኛለች፡፡  የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 3.63 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡ በተያያዘ የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን  በሴራሊዮን ለደረሰው ሽንፈት ምቹ ባልሆነ ስታድዬም ጨዋታ መደረጉ እንዲሁም የዳኝነት በደል መብዛቱን ምክንያት አድርገዋል፡፡ ይህን አስመልክቶም ለአፍሪካ የእግር ኳስ ፌደሬሽን የክስ ማመልከቻ ማስገባታቸው ታውቋል፡፡ በተጨማሪም የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያውን የሃራምቤ ኮከቦች በሽንፈት መጀመራቸው በፌደሬሽኑ አካባቢ የነበረው የአስተዳደር ቀውስ ቆስቁሶታል፡፡ በተለይ ከ2018 የቻን ውድድር አዘጋጅነት በተያያዘ ነው፡፡ የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከመንግስት ሙሉ ድጋፍ ባለማግኘቱ መስተንግዶው ማቀላጠፍ አልቻልኩም በሚል እያማረረ ነው፡፡ የካፍ ኮሚቴ ሰሞኑን በናይሮቢ በነበረው ጉብኝት በ2018 እኤአ የሚካሄደው 5ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ሊጀመር 6 ወራት ቢቀሩትም ኬንያ ሙሉ ለሙሉ ዝግጁ አለመሆኗን በመጥቀስ፤ ሌላ አስተናጋጅ በሚመርጥበት ሁለተኛ ዕቅድ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በ2020 እኤአ 6ኛውን ቻን እንድታዘጋጅ የተመረጠችው ኢትዮጵያ፤ እንዲሁም ሞሮኮና ኮትዲቯር በምትክነት መስተንግዶውን ለመረከብ ፍላጎት አላቸው። ኬንያ በአፍሪካ ዋንጫ ለአምስት ጊዜያት የተሳተፈችው በ1972፤ በ1988፤ በ1990፤ በ1992 እና በ2004 እኤአ ላይ ነበር፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ463 ነጥብ 74ኛ ላይ የምትገኝ ሲሆን ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 17.06 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
ከምድብ 6 የምድብ ማጣርያውን ለማለፍ ቅድሚያ ግምት የተሰጣት ጋና በአክራ ከተማ በፍፁም የጨዋታ ብልጫ ኢትዮጵያን 5ለ0 ማሸነፏ ብዙዎችን አላስደነቀም። ለጥቋቁሮቹ ክዋክብቶች ጎሎቹን በ10ኛው ደቂቃ ላይ አሳሞሃ ጊያን፤ በ15ኛው ደቂቃ ቦዬ፤ በ35ኛው ደቂቃ ኦፍሪ እንዲሁም ድዋሜና በ48ኛው እና በ70ኛው ደቂቃዎች ላይ አስመዘግበዋል፡፡ የጋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ኩዋሲህ አፒያህ በራስ መተማመን እንደሚያሳድግ የአገሪቱ ሚዲያዎች አውስተዋል፡፡ ጋና ከኢትዮጵያ በኋላ ለዓለም ዋንጫ የምታደርገውን ዝግጅት ቀጥላለች ሰሞኑን ከሜኬሲኮ ጋር ተገናኝታ 1ለ0 የተሸነፈች ሲሆን በቀጣይ ደግሞ ከአሜሪካ ጋር የምትጫወት ይሆናል፡፡  የአፍሪካ ዋንጫ ለ4 ጊዜያት ያሸነፈችው ጋና በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ678 ነጥብ 49ኛ ላይ የምትገኝ ሲሆን የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 55.17  ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡ በሌላ በኩል ለዋልያዎቹ የአፍሪካ ዋንጫ የማለፍ ተስፋ በጋና ባጋጠመው የመጀመርያ ጨዋታ ከባድ ሽንፈት የሚያበረታታ አልሆነም፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን 10 ጊዜ በመሳተፍ አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ሆናለች፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ265 ነጥብ 125ኛ ላይ የምትገኘ ሲሆን፤ የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 723ሺ ዩሮ ነው፡፡
ከመጀመርያው ዙር ጨዋታ በኋላ ምድብ 6ን ጋና በ3 ነጥብ እና በ5 የግብ ክፍያ ስትመራው ሴራሊዮን በ3 ነጥብ እና በ1 የግብ ክፍያ 2ኛ ሆናለች፡፡ ኬንያ በ1 የግብ እዳ ሶስተኛ ደረጃን ስትይዝ ኢትዮጵያ በ5 የግብ እዳ የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች፡፡ የምድብ ማጣርያው 2ኛ ዙር ጨዋታዎች ከ8 ወራት በኋላ ሲቀጥሉ ኢትዮጵያ ከሴራሊዮን እንዲሁም ኬንያ ከጋና ይገናኛሉ፡፡ ከ14 ወራት በኋላ  ደግሞ የ3ኛና የ4ኛ ዙር ጨዋታዎች በሁለት ሳምንት የደርሶ መልስ ትንቅንቅ  ሲቀጥሉ በመጀመርያ ጋና ከሴራሊዮን እንዲሁም ኢትዮጵያ ከኬንያ እንዲሁም ከ1 ሳምንት በኋላ በመልስ ጨዋታ ሴራሊዮን ከጋና እንዲሁም ኬንያ ከሴራሊዮን ይጫወታሉ፡፡ ከ15 ወራት በኋላ በ5ኛ ዙር ጨዋታ ኢትዮጵያ ከጋና እንዲሁም ኬንያ ከሴራሊዮን እንዲሁም በ6ኛ ዙር ጨዋታ ሴራሊዮን ከኢትዮጵያ ጋና ከኬንያ ይገናኛሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከሁለት ሳምንት በፊት አክራ ከተማ ላይ ከገጠመው የ5ለ0 ሽንፈት በኋላ ብዙ የትችት ሃሳቦች ተንፀባርቀዋል፡፡ ዋልያዎች በቂ ዝግጅት እያደረጉ አይደለም፡፡ በፌደሬሽኑ በኩል ተገቢውን ትኩረት ያጡም ይመስላል፡፡  ቀደምት ዋልያዎችም በየክለቦቻቸው ስኬታማ ቢሆኑም በብሄራዊ ቡድኑ ያላቸው ሚና መዳከሙ ብዙዎችን ያስገረመ ነው፡፡   ከደቡብ አፍሪካ መልስ ፕሪሚዬር ሊጉን በኮከብ ግብ አግቢነት ሪከርድ አስመዝግቦ ያሸነፈው ጌታነህ ከበደ፤ በግብፅ ሊግ ሁለት ክለቦች በግብ አዳኝነት እና በኮከብ ተጨዋችነት የተሳካላቸው ኡመድ እና ሽመልስ፤ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊሱ ሳላዲን እንዲሁም ሰሞኑን የሩስያውን ክለብ ለመቀላቀል የበቃው ጋቶች ፓኖም የዋልያዎቹ አባላት ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ ለወደፊቱ ብዙ ተግባራ መሰራት ይኖርባቸዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ስኬታማ እንዲሆን የፋይናንስ አቅሙ ማሟላት፤ ለተጨዋቾች የማበረታቻ ክፍያዎች ማዘጋጀት፤  የወዳጅነት ጨዋታ እና በቂ የዝግጅት መስጠት ተገቢ ነው፡፡

Read 2596 times