Monday, 12 June 2017 06:48

ህንድ በክብደቱ ከአለማችን 2ኛው የሆነውን ግዙፍ ሮኬት አመጠቀች

Written by 
Rate this item
(3 votes)

ህንድ በጠፈር ምርምር ቴክኖሎጂ ታሪኳ ከሰራቻቸው ሮኬቶች ሁሉ በግዙፍነቱና በክብደቱ አቻ እንደማይገኝለት የተነገረውንና በክብደት ከአለማችን ሮኬቶች ሁለተኛውን ደረጃ የሚይዘውን ጂኤስኤልቪ ማርክ 3 የተሰኘ ሮኬት በተሳካ ሁኔታ ወደ ጠፈር ማምጠቋን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
640 ቶን ክብደት እንዳለው የተነገረለት ይህ ግዙፍ ሮኬት፣ በጠፈር ምርምር ዘርፍ ለምታመጥቃቸው እጅግ ከባድ ሳተላይቶች በብዛት የአውሮፓ አገራት ሮኬቶችን ስትጠቀም ለነበረቺው ህንድ ትልቅ እመርታ መሆኑንና ከጥገኝነት በመጠኑም ቢሆን እንደሚያላቅቃት ተነግሯል፡፡
ህንድ በአለማቀፉ የሳተላይት ማምጠቅ ገበያ ያላትን ድርሻ ለማሳደግ በስፋት እየሰራች እንደምትገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ለአውሮፓ አገራት ሮኬቶች ከፍተኛ ክፍያ ከመክፈል የሚያድናትን ይህን ግዙፍ ሮኬት ሰርታ ለማምጠቅ መቻሏም ጥረቷ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የሚያመለክት ነው ብሏል፡፡
የ43 ሜትር ቁመት ያለው ግዙፉ የህንድ ሮኬት ከአለማችን በክብደቱ ሁለተኛው እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤በክብደት ክብረወሰኑን የያዘው የናሳው ሳተርን 5 ሮኬት እንደሆነም አክሎ ገልጧል፡፡
አገሪቱ ከቅርብ አመታት ወዲህ በጠፈር ምርምሩ መስክ ጉልህ የሚባሉ ውጤቶችን እያስመዘገበች ነው ያለው ዘገባው፣ ለውጤታማነቷ ማሳያ ይሆናሉ ብሎ ከጠቀሳቸው ስኬታማ ተግባራት መካከልም፣ ከወራት በፊት ወደ ማርስ ያደረገቺው የጠፈር ጉዞና በአንድ ተልዕኮ ከ100 በላይ ሳተላይቶችን ያመጠቀችበት አጋጣሚዎች እንደሚገኙበት አስታውሷል፡፡

Read 3060 times