Sunday, 04 June 2017 00:00

ደ/ ሱዳን ለ3ኛ ጊዜ የአለማችን ቀዳሚዋ መረጋጋት የራቃት አገር ሆናለች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  ኢትዮጵያ ባለመረጋጋት ከአፍሪካ 10ኛ ደረጃ፤ ፊንላንድ በመረጋጋት ከአለም 1ኛ ደረጃ ይዘዋል ተብሏል

      ፈንድ ፎር ፒስ የተባለውና ተቀማጭነቱ በአሜሪካ የሆነው የጥናት ተቋም በቅርቡ ይፋ ባደረገው የ2017 የዓለማችን አገራት ያለመረጋጋት ደረጃ ሪፖርት መሰረት፣ ደቡብ ሱዳን ከአለማችን መረጋጋት የራቃትና የመፈራረስ ከፍተኛ ዕድል ያላት ቀዳሚዋ አገር ሆናለች፡፡
አስራ ሁለት ያህል ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቁልፍ አመልካቾችን መሰረት አድርጎ የአለማችንን አገራት የመፈራረስ ዕድል ተጋላጭነት ደረጃ የሚያስቀምጠው ተቋሙ፣ በ2017 ሪፖርቱ ካካተታቸው 178 የአለማችን አገራት ደቡብ ሱዳንን እጅግ በከፋ ሁኔታ ላይ የምትገኝ ሲል በቀዳሚነት አስቀምጧታል፡፡ ባለመረጋጋት ከደቡብ ሱዳን ቀጥሎ በቅደም ተከተላቸው እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የአፍሪካ አገራት ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ቻድ፣ ጊኒ፣ ናይጀሪያ፣ ዚምባቡዌ እና ኢትዮጵያ መሆናቸውንም ሪፖርቱ ገልጧል፡፡
በተቋሙ ሪፖርት መሰረት፤ እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም በመረጋጋት ከአለማችን አገራት የአንደኛ ደረጃን የያዘቺው ፊላንድ ስትሆን፣ ኖርዌይ፣ ስዊዘርላንድ፣ ዴንማርክና አየርላንድ ይከተላሉ፡፡
ከፍተኛ ያለመረጋጋት ችግር ካለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሶማሊያ፣ መካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ የመንና ሶርያ እንደሚጠቀሱ የገለጸው ሪፖርቱ፣ ከአምናው ደረጃቸው አንጻር የመረጋጋት ሁኔታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ካሽቆለቆለባቸው የአለማችን አገራት መካከል ሜክሲኮ፣ ኢትዮጵያና ቱርክ እንደሚገኙበትና ኢትዮጵያ ባለመረጋጋትና ለመፈራረስ ተጋላጭ በመሆን ከአፍሪካ አገራት 10ኛ ደረጃ መያዟንም አመልክቷል፡፡
ተቋሙ አመታዊ ሪፖርቱን ማውጣት ከጀመረ 13 አመታት ያህል ቢሆነውም፣ ከአጠናን ስልቱ፣ ከሚዛናዊነቱና ሊገመቱ የሚችሉ ሁነቶችን ወይም ክስተቶችን ቀድሞ ከመተንበይ አቅሙ ጋር በተያያዘ በስፋት እንደሚተች ዘገባዎች ያመለክታሉ፡፡

Read 934 times