Monday, 20 March 2017 00:00

9 የታንዛኒያ ጋዜጠኞች ስለትራምፕ ሃሰተኛ መረጃ በማሰራጨታቸው ከስራ ታገዱ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

 ራፐሩ ስኑፕ ዶግ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ ቪዲዮ ለቋል

      የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የታንዛኒያውን አቻቸውን ጆን ማጉፋሊን በማድነቅ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎችን አጣጣሉ የሚል ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩ ቲቢሲ የተሰኘው የታንዛኒያ የብሮድካስቲንግ ተቋም ባልደረቦች የሆኑ 9 ጋዜጠኞች ከስራ መታገዳቸው ተዘግቧል፡፡
ጋዜጠኞቹ “ትራምፕ ሙጉፋሊን የአፍሪካ ጀግና ሲሉ የአመራር ብቃታቸውን በማድነቅ አሞካሽተዋቸዋል፣ ሌሎች የአፍሪካ መሪዎች ግን አንዳች እንኳን ፋይዳ ያለው ነገር እየሰሩ አይደለም ሲሉ ተናግረዋል” የሚለውን ሃሰተኛ መረጃ በማሰራጨታቸው ከስራ መታገዳቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ የተቀሩት የአፍሪካ መሪዎች ከታንዛኒያው ፕሬዚዳንት ሙጉፋሊ ሊማሩ ይገባል ብለዋል በማለት ሃሰተኛ መረጃ ያሰራጩት ጋዜጠኞቹ፤ ከሙጉፋሊ ብቃቶች መካከል ሙስናን በመዋጋት ረገድ ያሳዩት ቁርጠኝነት አንዱ ነው ማለታቸውንም አትተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ደግሞ ታዋቂው ራፐር ስኑፕ ዶግ፤ ዶናልድ ትራምፕን ተኩሶ ሲገድላቸው የሚያሳይ የሙዚቃ ቪዲዮ ሰሞኑን መልቀቁን ተከትሎ፣ ፕሬዚዳንቱ “ስኑፕ ዶግ በዚህ አጉል ድርጊቱ ሳቢያ ሊታሰር ይገባል” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡
ትራምፕ በትዊተር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ስኑፕ ዶግ በቪዲዮው ሲገድል ያሳየው ኦባማን ቢሆን ኖሮ ወደ እስር ቤት ነበር የሚገባው ማለታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የትራምፕ የግል ጠበቃ ማይክል ኮሄን በበኩላቸው ቪዲዮውን ሲመለከቱ በእጅጉ መደንገጣቸውን በማስታወስ፣ ስኑፕ ዶግ ፕሬዚዳንቱን አዋርዷል ይቅርታ ሊጠይቃቸው ይገባል ማለታቸውን ገልጧል፡፡

Read 3123 times