Monday, 20 March 2017 00:00

በአማራ ክልል ከ800 በላይ አመራሮች የሙስና ጥቆማ ቀርቦባቸዋል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(24 votes)

 አጣሪ ኮሚቴ ተቋቁሞ ጉዳዩ እየተጣራ ነው
           የአማራ ክልላዊ መንግስት 462 ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ከ800 በላይ አመራሮች ላይ የሙስና እና ተያያዥ ችግሮችን የተመለከቱ ጥቆማዎች ከህዝቡ ቀርቦለት እየመረመረ መሆኑን አስታወቀ፡፡  
የክልሉ መንግስት ኮሚኒኬሽን ኃላፊ አቶ ንጉሡ ጥላሁን ሰሞኑን የክልሉ ም/ቤት ያደረገውን መደበኛ ጉባኤ አስመልክቶ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤462 የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና 362 መካከለኛ አመራሮች ከህዝቡ “በድለውናል” የሚል አቤቱታና ጥቆማ ቀርቦባቸው በአስቸኳይ ጉዳዩ እንዲጣራ የሰሞኑ ጉባኤ ወስኗል ብለዋል። ጉዳዩን አጣሪ ኮሚቴም መቋቋሙን አቶ ንጉሡ አስታውቀዋል፡፡ የከፋ የሙስና ወንጀል የተገኘባቸው አመራሮች፣ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ጉዳያቸውን ይዞ እንዲመረምር እንደሚደረግም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል ብአዴን የቀድሞ የጎንደር ከተማ ከንቲባ አቶ ጌትነት አማረን ከማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነት ማባረሩንና የቀድሞ የአዊ ዞን አስተዳደር እና የወጣቶችና ስፖርት ኃላፊ የነበሩትን አቶ ባዘዘው ጫኔን ጨምሮ ለሶስት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ከባድ ማስጠንቀቂያ መስጠቱን  የኮሙኒኬሽን ሃላፊው ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡ የክልሉ መንግስት “በጥልቅ ተሃድሶው” የተለያዩ ችግሮችና ድክመቶች አሉባቸው ያላቸውን ከአንድ ሺህ በላይ አመራሮቹን ማባረሩም ታውቋል፡፡  
የሰሞኑ የብአዴን ጉባኤ አወዛጋቢውን የወልቃይት ጉዳይ ተወያይቶበት እንደሆነ የተጠየቁት አቶ ንጉሱ፤“የወልቃይት ጉዳይ የአማራ ክልል ዋነኛው ጉዳይ መሆን የለበትም፣ጥያቄው መቅረብ ያለበት ለትግራይ ክልል መንግስት ነው” የሚል ውሳኔ ቀደም ሲል መወሰኑን ጠቁመው፣ የትግራይ ክልል መንግስት ይሄን ተገንዝቦ፣ህዝቡን ማዕከል አድርጎ ምላሽ እንዲሰጥ ይጠበቃል፤ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ላይ ጉባኤው አልተወያየም ሲሉ መልሰዋል፡፡   

Read 5341 times