ባለፈው ዓመት ሃና እና ዳንኤል የተባሉ ኢትዮጵያውያን የተሳተፉበት የ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ውድድር ከሁለት ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር የተገለፀ ሲሆን በዘንድሮ ውድድር ኢትዮጵያውያን እንደማይሳተፉ ታውቋል፡፡ ዘንድሮ ለ7ኛ ጊዜ በሚካሄደው ውድድር ለአሸናፊው የሚሰጠው የገንዘብ ሽልማት ወደ 300ሺ ዶላር (ከ3ሚ. ብር በላይ) ማደጉን የጠቆመው “ቢግ ብራዘር አፍሪካ”፤ ሽልማቱ ያደገው ከኮካኮላ በተገኘው የስፖንሰር ሺፕ ድጋፍ ነው ብሏል፡፡
በደቡብ አፍሪካው የመዝናኛ ኩባንያ ኤንዴሞል እና በብሮድካስት ተቋሙ ኤም ኔት ትብብር የሚዘጋጀው ውድድር፤ በዲኤስቲቪ ቻናል ለ24 ሰዓት በቀጥታ ስርጭት የሚተላለፍ ሲሆን ውድድሩ ለ91 ቀናት አብሮ የመኖር ፉክክር እንደሆነ ይታወቃል፡፡ከ48 ቀናት በኋላ የሚጀመረው የ”ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ውድድር በ47 አገራት ቀጥተኛ የቴሌቪዥን ስርጭት የሚኖረው ሲሆን ከላይቤርያና ከሴራሊዮን አዳዲስ ተወዳዳሪዎች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል፡፡