Monday, 05 December 2016 09:43

ሆሄ የስነ ፅሁፍ ሽልማት አወዳደር ሊሸልም ነው

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ባለፈው 1 ዓመት የታተሙ መፃህፍት ይወዳደራሉ
     በረዥም ልቦለድ፣ በግጥምና በልጆች መፃህፍት ዘርፍ የሥነ ፅሁፍ ሥራዎች ተወዳድረው ሊሸለሙ ነው።
ኖርዝ ኢስት ኤቨንትስ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከብሄራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መፃህፍት ኤጀንሲ ጋር በትብብር ያዘጋጁት ሆሄ የሥነፅሁፍ ሽልማት ፕሮግራም፤ አሸናፊ ደራስያንን ከመሸለም ባሻገር የንባብ ባህል እንዲስፋፋ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ላበረከቱ ክበባትንና ቤተ መፃህፍትም የሚመሰገኑበትና ዕውቅና የሚያገኙበት ይሆናል ተብሏል፡፡
የሽልማት ፕሮግራሙ አዘጋጆች ከትናንት በስቲያ በጎተ ኢንስቲትዩት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤ ለውድድር የሚቀርቡት መፃህፍት ከመስከረም 1 ቀን 2008 እስከ ጳጉሜ 5 ቀን 2008 ዓ.ም ድረስ የታተሙ መሆን አለባቸው፡፡ ተወዳዳሪ መፃህፍቱ በዳኞች ኮሚቴ በተዘጋጀላቸው መስፈርቶች መሰረት የሚመዘኑ ሲሆን በዳኞች ኮሚቴ ከሚሰጠው ውጤት በተጨማሪ አንባቢያን በነፃ የስልክ መልዕክትና በድረ ገፅ የሚሰጡት ድምፅም የተወሰነ ነጥብ ይኖረዋል ተብሏል። አጠቃላይ ውጤቱ የሚታወቅ ይሆናል፡፡
በውድድሩ መሳተፍ የሚፈልጉ ደራሲያን ከታህሳስ 4-19 2009 ዓ.ም ሞርኒንግ ስታር ሞል ላይ በሚገኘው የድርጅቱ ቢሮ፣ በጎታ ኢንስቲቲዩትና በቡክላይት መፅሀፍ መደብር መመዝገብ እንዳለባቸው የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ የሽልማት ስነ ስርዓቱ በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ እንደሚካሄድ ተናግረዋል፡፡

Read 1818 times