Monday, 05 December 2016 08:51

ፍ/ቤት እነ ሃብታሙ አያሌውን ከክስ ነፃ አደረጋቸው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(5 votes)

    አብርሃ ደስታና ዳንኤል ሺበሺ ተከላከሉ ተብለዋል
          
     በከፍተኛ ፍ/ቤት ከቀረበባቸው የሽብር ክስ በነፃ ከተሰናበቱ በኋላ አቃቤ ህግ ይግባኝ ከጠየቀባቸው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች መካከል ሃብታሙ አያሌውን ጨምሮ ሶስቱ በነፃ የተሠናበቱ ሲሆን ሁለቱ ተከላከሉ ተብለዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ የቀድሞ አመራር አቶ ሃብታሙ አያሌው፤ በከፍተኛ ህመም እየተሰቃዩ መሆኑን በመግለፅ የተጣለባቸው የጉዞ እገዳ ተነስቶ ወደ ውጭ ሃገር ሄደው እንዲታኩመ በተደጋጋሚ ሲጠይቁ የነበረ ቢሆንም አዎንታዊ ምላሽ ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ የጠቅላይ                ፍ/ቤት ሠበር ሠሚ ችሎት ትናንት በሠጠው ብይን፣ አቶ ሃብታሙ የተጣለባቸው እገዳ መነሣቱንና ከቀረበባቸው ክስም ነፃ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ይግባኝ ተጠይቆባቸው ከነበሩ የተቃዋሚ አመራሮች መካከል የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሸዋስ አሠፋን ጨምሮ የፓርቲ አባል ያልሆኑት አቶ አብርሃም ሠለሞን ጠቅላይ ፍ/ቤቱ በነፃ ያሠናበታቸው ሲሆን የአረና አመራር አባሉና የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ  መምህሩ አብርሃ ደስታ እንዲሁም የቀድሞ የ‹‹አንድነት›› የድርጅት ጉዳይ ም/ሃላፊ የነበሩትና  በቅርቡ በኮማንድ ፖስቱ በቁጥጥር ስር ውለው በእስር ላይ የሚገኙት አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የቀረበባቸውን የሽብር ክስ መከላከል ያስፈልጋቸዋል ተብለዋል፡፡
በፍ/ቤቱ ውሳኔ ላይ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የተከሳሾቹ የህግ አማካሪና ጠበቃ አመሀ መኮንን፤ ተከላከሉ የተባሉት አቶ አብርሃ ደስታና አቶ ዳንኤል ሺበሺ ጉዳያቸው ቀድሞ ወደነበረው የከፍተኛው ፍ/ቤት እንደሚመለስ ጠቁመው፤ በቀረበባቸው ክስ ላይ መከላከያ ማስረጃ በማቅረብ ክርክራቸውን እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል፡፡
የፀረ ሽብር አዋጁ በማንኛውም ሁኔታ የዋስ መብት እንደማይፈቅድ የገለፁት አቶ አመሃ፤ የተለየ ነገር ካልተፈጠረ በስተቀር ተከላከሉ የተባሉ በድጋሚ በእስር ላይ ሆነው ጉዳያቸውን ሊከታተሉ እንደሚችሉ አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አቃቤ ህግ ወደ ከፍተኛው ፍ/ቤት በመሄድ ተዘግቶ የነበረውን መዝገብ በድጋሚ እንደሚያንቀሳቅስና መጥሪያ ሲደርሳቸው ፍ/ቤት እንደሚቀርቡ አቶ አመሃ አብራርተዋል፡፡
በህመም ላይ የሚገኙት አቶ ሃብታሙ አያሌው፤ ከዚህ በኋላ ምንም አይነት የጉዞ እገዳ እንደሌለባቸውና ወደ ውጭ አገር ሄደው መታከም እንደሚችሉ ታውቋል፡፡

Read 4231 times