Sunday, 13 November 2016 00:00

በ16ኛው ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

• 42 ሺህ ተሳታፊዎች
 • የቻይናዋ ኦሎምፒክ ሻምፒዮን ዢን ዋንና የደቡብ አፍሪካው ማራቶን ሯጭ ሄነሪክ ራማላ
 እንግዶች ናቸው
   • 6ሺ በቀይ መነሻ 36ሺ በአረንጓዴ መነሻ
      • 500 አትሌቶች፤ 250 ቱሪስት ሯጮች፤ 20 አምባሳደሮች፤30 የአካል ጉዳተኞች፤ 500 የበጎ
         ፍቃድ አገልጋዮች እንዲሁም 30 አርቲስቶች
          • ባለፈው ዓመት ከ750 ውጭ ቱሪስት ሯጮች 1.803 ሚ ዶላር የኢኮኖሚ አስተዋፅኦ

    በቀጣይ ሳምንት መነሻ እና መድረሻውን በመስቀል አደባባይ  አድርጎ በሚካሄደው 16ኛው ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 42 ሺህ ስፖርኞች ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡ የታላቁ ሩጫ ዲያሬክተር ለዝግጅት ክፍላችን በላኩት መግለጫ እንዳስታወቁት ‹‹መስቀል አደባባይ ትልቁ ምልክታችን ነው፡፡ ውድድሩን በዚህ እንድናደርግ ስለተፈቀደልን ትልቅ ደስታ ይሰማናል፡፡ ከስራችን ውስጥ አንዱና ዋንኛው የአገራችንን ገፅታ መገንባት ነው›› ብለዋል፡፡ የ 10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው መነሻው በመስቀል አደባባይ ሆኖ በስታዬም፤ በሜክሲኮ፤ በአፍሪካ ህብረት አደባባይ፤ ሳር ቤት፤ ቄራ፤ ጎተራ ማሳለጫ፤ ላንቻ፤ መሳለሚያ በማድረግ በመስቀል አደባባይ ይፈፀማል፡፡
በ2008 እኤአ በቤጂንግ ኦሎምፒክ በ3ሺ መሰናል የኦሎምፒክ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችውና በቻይና የናይኪ ክለብ ፕሬዝዳንት የሆነችው የቻይናዋ አትሌት ዢን ዋን እና ታዋቂው የረጅም ርቀት፤ የማራቶን ሯጭ የሀጎነው የደቡብ አፍሪካው ሄንድሪክ ራማላ በክብር እንግድነት የሚገኙ ሲሆን ታዋቂው የደቡብ አፍሪካ የብሮድካት ኩባንያ ሱፕር ስፖርት የ52 ደቂቃዎች ስርጭት እንደሚሰራ ታውቋል፡፡
የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው በሁለት ምድብ በተካፋፈለ አዲስ አሯሯጥ መደረጉ ልዩ ያደርገዋል፡፡ የመጀመርያዎቹ በቀይ መነሻ የሚሮጡትና ከ1 ሰአት ባነሰ ጊዜ ውስጥ 10 ኪሎ ሜትሩን የሚጨርሱ ሲሆን ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አዘጋጆች በደረሰን መረጃ በዚሁ ምድብ ለመሮጥ የተመዘገቡት ብዛታቸው 6000 ነው።  በሌላ በኩል በሁለተኛው ምድብ በአረንጓዴ መነሻ ለመሮጥ 36ሺ ተሳታፊዎች መመዝገባቸውን ያመለከቱት አዘጋጆቹ፤ በዚህ ምድብ ውድድሩን ለመጨረስ ከ1 ሰአት በላይ ጊዜ የሚወስድባቸውና በፌስቲቫል መልኩ የተለያዩ ትርኢቶችን እያሳዩና እየተዝናኑ የሚሮጡ እንደሚገኙበት ገልፀዋል፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ቢሮ ለስፖርት አድማስ በላከው መግለጫ እንደተጠቆመው ዘንድሮ በውድድሩ ላይ 500 አትሌቶች በዋናው ውድድር ተሳታፊ ሲሆኑ ከ300ሺ ብር በላይ ለሽልማት መዘጋጀቱ ታውቋል፡፡ በአጠቃላይ በ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው ከሚሳተፉት 42ሺ ተሳታፊዎች መካከል 15ሺ ያህሉ በግል፤ 24ሺ በተለያዩ ድርጅቶች፤ 600 በሞባይል ባንኪንግ ለተሳትፎ መመዝገባቸውን የጠቀሰው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መረጃ፤ 20 የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች፤ 30 የአካል ጉዳተኞች፤ 500 የበጎ ፍቃድ አገልጋዮች እንዲሁም 30 አርቲስቶች ‹‹ሌሎችን ለመርዳት እሮጣለሁ›› የሚለውን ዓላማ በማንገብ ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡
የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫውን ለሶስት አመታት አብይ ስፖንሰር የሆነው ቶታል ኢትዮጵያ ሲሆን ከ15 በላይ የተለያዩ ስፖንሰሮችን ያሰባሰበ ውድድር እንደሆነም ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል በ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫው  ከውጭ አገር የሚመጡት ተሳታፊዎች ብዛት 250 ሲሆኑ ለመጀመርያ ጊዜ የቻይና ስፖርተኞችም እንደሚገኙ  ታውቋል፡፡ ዘንድሮ የውጭ አገር ተሳታፊዎች ብዛት የቀነሰው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መውጣቱን ተከትሎ የብዙ አገራት ኤምባሲዎች ለዜጎቻቸው በሰጡት ማስጠንቀቂያ ተሳትፏቸውን ለመሰረዝ በመወሰናቸው ነው፡፡
ይሁንና የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድር በቱሪዝም ገቢ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ የላቀ አስተዋፅኦ እንዳለው  በሊድስ ቢኬትዩኒቨርስቲ የተሰራው አንድ ጥናት ማረጋገጡን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ በዩኒቨርስቲው ለካርኒጄ ሪሰርች ኢንስትቲዩት The Economic Impact of International Tourists attending the 2015 Great Ethiopian Run በሚል ርእስ በዶክተር ኢያን ሪቻርድስ የተሰራው ጥናት እንዳመለከተው ባለፈው ዓመት በ15ኛው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ውድድር 750 የውጭ አገር ዜጎች ተሳትፈው በተለያዩ ወጭዎች እና ለበጎ አድራጎት በሰጡት መዋጮ ከ1.803 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ አስተዋፅኦ አድርገዋል። በጥናታዊ ሪፖርቱ ላይ በዝርዝር እንደተገለፀው 750ዎቹ ቱሪስት ሯጮች ለሆቴል፤ ለአየር ትኬት በተለያዩ ሁኔታዎች በድምሩ 803ሺ ዶላወጭ ሲያደርጉ ከመካከላቸው 38 በመቶ ያህሉ በበጎ ፍቃድ የገቢ ማሰባሰብ እንቅስቃሴ በመሳተፍ 1 ሚሊዮን ዶላር አዋጥተው ለተለያዩ የእርዳታ ድርጅቶች እንዲበረከት አድርገዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የ2009 የፕላን ኢንተርናሽናል የልጆች ውድድር የዛሬ ሳምንት በወጣቶችአካዳሚ እንደሚካሄድም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የልጆች ውድድሩ በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ10 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር ዋዜማ ሲካሄድ  በሶስት የእድሜ መደቦች ከ11 ዓመት በታች፤ ከ8 አመት በታ እና ከ5 ዓመት በታች ተካፍሎ ሲደረግ ከ4500 በላይ ህፃናና ታዳጊዎችን በማሳተፍ እንደሆነ ታውቋል፡፡

Read 1223 times