Monday, 26 September 2016 00:00

የቀድሞው የብራዚል መሪ በ1.14 ሚ. ዶላር ሙስና ፍ/ ቤት ይቀርባሉ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

   የቀድሞው የብራዚል ፕሬዚዳንት ሉላ ዳ ሲልቫ ከታዋቂው የአገሪቱ የነዳጅ ኩባንያ ፔትሮባርስ 1.14 ሚሊዮን ዶላር በጉቦ መልክ መቀበላቸው በመረጋገጡ የቀረበባቸው የሙስና ክስ በፍርድ ቤት ተቀባይነት ማግኘቱንና በቅርቡ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ መባሉን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በ70 አመቱ ዳ ሲልቫ ከነዳጅ ኩባንያው ጋር የተጠቀሰውን ገንዘብ በጉቦ መልክ መቀበላቸውንና ኦኤኤስኤስኤ ከተባለው የአገሪቱ የኮንስትራክሽን ኩባንያ ጋር በተያያዘ የሙስና ወንጀል መፈጸማቸው በበቂ ማስረጃዎች መረጋገጡን የጠቆመው ዘገባው፤የዳ ሲልቫ ሚስትና ሌሎች ስድስት ግለሰቦችም በሙስና ወንጀሉ ተሳታፊ ናቸው መባላቸውንም ገልጧል፡፡
ዳ ሲልቫ ሶስት የሙስና እና አንድ የገንዘብ ማጭበርበር ክሶች እንደተመሰረቱባቸው ያመለከተው ዘገባው፤ የቀረቡባቸው ክሶች እያንዳንዳቸው ከ10 እስከ 16 አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት የሚያስጥሉ እንደሆኑም ጠቁሟል። ብራዚልን እ.ኤ.አ ከ2003 እስከ 2011 ያስተዳደሩት ሉላ ዳ ሲልቫ የቀረበባቸውን የወንጀል ክስ በመቃወም፣ የተባለውን የወንጀል ድርጊት በፍጹም አልፈጸምኩም፤ የውሸት ክስ ነው የተመሰረተብኝ በማለት ክደዋል ተብሏል፡፡
ፔትሮባርስ ከተባለው የአገሪቱ የነዳጅ ኩባንያ ጋር በተያያዘ የተፈጸመውንና በኩባንያው ባለአክሲዮኖችና በግብር ከፋዩ ህዝብ ላይ የ12.6 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ያስከተለውን ከፍተኛ የሙስና ቅሌት በተመለከተ ላለፉት ሁለት አመታት ምርመራ ሲደረግ መቆየቱንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 2558 times