Monday, 26 September 2016 00:00

ተቃዋሚዎች፤ የባለስልጣናት ለውጥ የህዝብ ጥያቄን አይመልስም አሉ

Written by 
Rate this item
(47 votes)

‹‹የህዝቡ ጥያቄ የስርአትና የፖሊሲ ለውጥ ነው››

   በተሃድሶ ግምገማ ላይ ከሚገኙት አራቱ የኢህአዴግ ድርጅቶች ኦህዴድ ሊቀመናብርቱን ሰሞኑን ከሃላፊነት ያነሰ  ሲሆን  ተቃዋሚ ፓርቲዎች  በየትኛውም ደረጃ የሚደረጉ የአመራር ለውጦች ለህዝብ መሰረታዊ ጥያቄ ምላሽ አይሆኑም ብለዋል፡፡
ህዝብ የጠየቀው የስርዓትና የፖሊሲ ለውጥ እንጂ የግለሰቦች መቀያየርን አይደለም፤ ይላሉ ተቃዋሚዎች፡፡
የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ የገዥውን ፓርቲ ተሃድሶ ብቻ ሳይሆን ሁሉም አስተሳሰቦች የተካተቱበት የፖሊሲ ለውጦች ነው የጠየቅነው ብለው፡፡ አሁን  ባለው ፖሊሲ ላይ ግለሰቦችን መለዋወጥ ተሃድሶ እንደማይሆን ተናግረዋል፡፡ ‹‹የህዝቡ ጥያቄም የአመራሮች መለዋወጥ›› አይደለም ያሉት ዶ/ር ጫኔ፤ ተሃድሶው በዚህ መልኩ ከቀጠለ ምንም ለውጥ አያመጣም፤ የህዝቡንም ጥያቄ በዚህ መንገድ መመለስ አይቻልም ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ የኦህዴድ አመራሮች መቀያየራቸው ሌሎቹ ድርጅቶችም ከዚህ የተለየ አጀንዳ እንደሌላቸው ያሳያል፡፡ ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በኢዴፓ እምነት ይህ አካሄድ የበለጠ የህዝበን ጥያቄ የማፈኛ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ አዴፓ አሁንም ብቸኛው መፍትሄ የብሄራዊ እርቅ መድረክ ማዘጋጀት ነው የሚል አቋም እንዳለውም ዶ/ር ጫኔ ተናግረዋል፡፡
በመጀመሪያም ቢሆን ህዝብ የአመራር ለውጥ አልጠየቀም ያሉት የሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው፤ ‹‹ጥያቄው አጠቃላይ የስርአት ለውጥ ነው›› ብለዋል፡፡ ‹‹ህዝቡ ድርጅቶቹና ፖሊሲያቸው አይወክለንም፤ አያስፈልገንም ነው ያለው፤ ግለሰቦች ይለወጡ አላለም›› ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ ድርጅቶቹ በህዝብ ያልተጠየቁትን ነው መልስ እየሰጠን ነው የሚሉት ብለዋል፡፡
ህዝቡ ጉዳዩ ከግለሰቦች ሳይሆን ከስርአቱ ጋር ነው፤ የሚሉት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ም/ሊቀመንበርና የመድረክ አመራር አቶ ሙላቱ ገመቹ በበኩላቸው፤ የህዝቡን ጥያቄዎች ያላገናዘበ መፍትሄ ነው ለመስጠት እየተሞከረ ያለው ብለዋል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ከግለሰብ አመራሮች ጋር ችግር የለበትም፤ መሻሻል ያለበት የመንግስት ስርአትና መዋቅር ነው ሲሉ በአፅንኦት የገለፁት አቶ ሙላቱ፤ አሁን የተያዘው የመፍትሄ አቅጣጫ ብዙ ርቀት የሚያስኬድ አይሆንም ብለዋል፡፡
ድርጅቶቹ ከመሰረታዊው የህዝብ ጥያቄ ለመሸሽ በሌላ ጉዳይ ላይ ጊዜያቸውን እያጠፉ ነው፤ ያሉት የመኢአድ ፕሬዚዳንት ዶ/ር በዛብህ ደምሴ፤ ማድረግ ያለባቸው ፖሊሲያቸውን መመርመርና መቀየር ነው ብለዋል፡፡
ለተፈጠሩት ችግሮች በሙሉ ተጠያቂው የመንግስት ፖሊሲ እንጂ የፖሊሲው አስፈፃሚ ግለሰቦች ሊሆኑ አይችሉም የሚሉት ፕሬዚዳንቱ መንግስት የፖሊሲ ማሻሻያዎችን ማድረግ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
አራቱ የኢህአዴግ ድርጅቶች፡- ብአዴን፣ ህውሓት፣ ኦህዴድና  ደኢህዴን በየክልሎቻቸው የተሃድሶ ግምገማ ሲያደርጉ የሰነበቱ ሲሆን በግምገማው በርካታ የአመራር ለውጦች ይጠበቃሉ ተብሏል፡፡ ኦህዴድ የቀድሞ አመራሮቹን አቶ ሙክታር ከድርና ወ/ሮ አስቴር ማሞን ካሃላፊነት አንስቶ በምትካቸው አቶ ለማ መገርሳና ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁን የተካ ሲሆን አቶ ለማ መገርሳ የክልሉ ፕሬዚዳንት እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡
አዲሱ የኦህዴድ ሊቀመንበር አቶ ለማ መገርሳ በተሾሙ ማግስት በአጭር የሞባይል መልዕክት ለህዝብ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ድርጅታቸው የሰፊውን ህዝብ ጥያቄ በየደረጃው ተሃድሶ በማድረግ እንደሚመልስ አስታውቀዋል፡፡ በመቀጠል በላኩት ሌላ የሞባይል መልዕክት ደግሞ፤ ኦህዴድ በህዝብ ፍላጎት ላይ ተመስርቶ ለማድረግ የወሰነው ጥልቅ ተሃድሶ ለሌላውም አርአያ የሚሆን እርምጃ ነው፤ ኦህዴድ ሁሌም ከህዝብ ጎን ይቆማል ብለዋል፡፡


Read 8889 times