Sunday, 11 September 2016 00:00

በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ለደረሰው የህይወት መጥፋት መኢአድ መንግስትን ተጠያቂ አደረገ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(25 votes)

የእርቅ መንግስት እንዲመሰረት ፓርቲው ጠይቋል

ባለፈው ሳምንት በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በተነሳው የእሳት ቃጠሎ ለደረሰው የህይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት መንግስትን  ተጠያቂ ያደረገው የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፤ ጉዳዩ በገለልተኛ አካል እንዲጣራ ጠይቋል፡፡
ፓርቲው ሰሞኑን በፅ/ቤቱ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤መንግስት በአደጋው 23 ታራሚዎች መሞታቸውን ቢናገርም ቁጥሩ ከተጠቀሰው በላይ ሊሆን እንደሚችል ጥርጣሬ አለኝ ብሏል፡፡
መንግስት ለታራሚዎች ህገ መንግስታዊ ከለላ በመስጠት ደህንነታቸውን መጠበቅ ሲገባው፤ ይህ ሳይፈፀም መሞታቸውም ሆነ ድርጊቱ ከተፈፀመ በኋላ ለታሳሪ ቤተሰቦች ግልፅና የማያሻማ ፈጣን መልስ በመስጠት ፈንታ በቤተሰብ ላይ ከፍተኛ ጭንቀትና አሳዛኝ መጉላላት እንዲደርስ መደረጉን በጥብቅ አወግዛለሁ ብሏል መኢአድ፡፡ በጉዳቱ በደረሰው የሰው ህይወት መጥፋት ማዘኑንም ፓርቲው አስታውቋል፡፡
ፓርቲው በመግለጫው፤ በማረሚያ ቤቱ የደረሰውን ጉዳት ጨምሮ በአማራና ኦሮሚያ ክልል የደረሡ ጉዳቶች በገለልተኛ ወገን እንዲጣራ፣ ለጠፋው ህይወት መንግስት በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቅና የደም ካሣና የዜጎች ማቋቋሚያ ካሣ እንዲከፍል  ጠይቋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሣለኝ ነሀሴ 24 የሠጡት መግለጫ ‹‹ጦርነት ከማወጅ የማይተናነስ አሳዛኝም አስደንጋጭም ተግባር ነው›› ያለው ፓርቲው፤ በአስቸኳይ ትዕዛዙ እንዲሠረዝ አሳስቧል፡፡ ፓርቲው ከግጭቶችና ተቃውሞዎች ጋር በተያያዘ የታሠሩ እንዲፈቱና መንግስት ከተለያዩ ፓርቲዎች ጋር ውይይት በማካሄድ የዕርቅ መንግስት እንዲመሰረት ጠይቋል፡፡
አንጋፋ የኢህአዴግ አመራሮች ሠሞኑን በኢቢሲ እየሰጡ ያሉትን ማብራሪያ፣ አዲስ የመፍትሄ ሃሳብ ያፈለቀና ችግሩን አግባቡ የተረዳ አይደለም ሲል ፓርቲው አጣጥሎታል፡፡
የቂሊንጦ ማረምያ ቤት ቃጠሎን ተከትሎ በህይወት ያሉ ታራሚዎች ወደ ዝዋይ፣ ሸዋ ሮቢትና አዲስ አበባ ማረሚያ ቤቶች መዘዋወራቸውን ታውቋል፡፡   



Read 6662 times