Sunday, 21 August 2016 00:00

ፕሬዚዳንት ሙላቱና የመኢአድ አመራሮች በወቅታዊ ችግሮች ዙሪያ ተወያዩ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(51 votes)

በ25 ዓመት ውስጥ መሰል ውይይት ሲደረግ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው
‹‹ፕሬዚዳንቱ ሁሌም በሬ ክፍት ነው ብለውናል›› - ዶ/ር በዛብህ ደምሴ

ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፤ በአማራና በኦሮሚያ ክልል በተፈጠሩ ተቃውሞዎችና ግጭቶች እንዲሁም በአዲስ አበባ ቤት በፈረሠባቸው ነዋሪዎች ጉዳይ ዙሪያ የመኢአድ አመራሮችን በቤተመንግስታቸው ጠርተው አነጋገሩ፡፡
የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በቅርቡ ለፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሣለኝ፣ ለህዝብ ተወካዮችና ለፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ-ጉባኤዎች በፃፈው ደብዳቤ፤ በኦሮሚያና በአማራ ክልል በተፈጠሩ ተቃውሞዎችና ግጭቶች እንዲሁም በአዲስ አበባ ቤት በፈረሠባቸው ነዋሪዎች ጉዳይ ዙሪያ መንግስት ችግሩን መርምሮ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲያበጅ መጠየቁ ይታወሳል፡፡
ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ፤ ለፓርቲው ማሳሰቢያዎች ፈጣን ምላሽ በመስጠት ደብዳቤው በደረሳቸው በ4ኛው ቀን ወደ ፓርቲው ፅ/ቤት ስልክ አስደውለው ለውይይት እንደጋብዟቸው የመኢአድ ፕሬዚዳንት ዶ/ር በዛብህ ደምሴ ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
በተያዘላቸው ቀጠሮ መሠረትም የፓርቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር በዛብህ ደምሴና ተ/ም/ፕሬዚዳንት አቶ አሠፋ ሃብተወልድ፣ ከፕሬዚዳንቱ ጋር ለ1 ሰዓት ተኩል የቆየ ውይይት በቤተ መንግስት አድርገዋል፡፡
በውይይታቸውም በተለይ በአዲስ አበባ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ፣ ህገ ወጥ ተብለው የፈረሡ ቤቶች፤ ህገ ወጥ ናቸው ቢባሉ እንኳ ያለ በቂ ዝግጅትና ውይይት እንዲሁም በክረምት መፍረሳቸው አግባብ አለመሆኑን የፓርቲው አመራሮች እንዳነሱላቸው ጠቅሰው፤  ፕሬዚዳንቱም “ቤቶቹ በክረምት መፍረስ አልነበረባቸውም” ማለታቸውን አመልክተዋል፡፡ ‹‹እስካሁን በፈረሡት ላይ ምንም ማድረግ አይቻልም፤ በቀጣይ እንዲህ አይነቱ ድርጊት እንዲቆም ይደረጋል፤ ቤታቸው የፈረሠባቸውንም መንግስት የትም አይጥላቸውም›› የሚል በተስፋ የተሞላ ምላሽ ፕሬዚዳንቱ እንደሠጡ ዶ/ር በዛብህ ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡
በአማራ ክልል በተለይ ከወልቃይት የማንነት ጥያቄ ጋር እንዲሁም በኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ፊንፊኔ ዙሪያ ማስተር ፕላን ጋር በተያያዘ የተቀሰቀሱ ተቃውሞና ግጭቶችን በተመለከተም ከፕሬዚዳንቱ ጋር ሰፊ ውይይት መደረጉ ተገልጿል፡፡
የፓርቲው አመራሮች በሁለቱ ክልሎች ያሉ ችግሮች በጥይትና በሃይል ሣይሆን በሠላማዊ መንገድ መፈታት እንዳለባቸው ያሳሰቡ ሲሆን ዶ/ር ሙላቱም ሀሳቡን እንደሚቀበሉና ችግሮች ሁሉ በውይይት መፈታት አለበት ብለው እንደሚያምኑ መግለፃቸውን ዶ/ር በዛብህ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
በአንድ ወቅት የሰለጠነችና የተረጋጋች አገር የነበረችው ሶርያ፤ ችግሮቿን በውይይት ለመፍታት ባለመሞከሩ፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቿ ለሞትና  ለስደት መዳረጋቸው በእጅጉ እንደሚያሳዝናቸው የተናገሩት ዶ/ር ሙላቱ፤ በኢትዮጵያ የሚነሱ ማናቸውም የህዝብ ጥያቄዎች በውይይት በመግባባት መፈታት አለባቸው የሚል እምነት እንዳላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
“ከፕሬዚዳንቱ ጋር በጥሩ መግባባት ፍሬያማ ውይይት አድርገናል” ያሉት የመኢአድ ፕሬዚዳንት ዶ/ር በዛብህ፤ “በ25 ዓመት የፓርቲው ታሪክ ውስጥ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ድምፃችንን ሰምቶ “ኑ እንወያይ” በማለት ሲያነጋግረን የመጀመሪያችን ነው” ብለዋል፡፡
መኢአድ ለችግሮች ሁሉ መፍትሄው ሰላማዊ ውይይት ብቻ ነው ብሎ እንደሚያምን የተናገሩት ዶ/ር በዛብህ፤ ከፕሬዚዳንቱ ጋር ያደረግነው ውይይት በአገሪቱ የፖለቲካ መድረክ በጎ ጅማሮ የሚባል ነው ሲሉ አወድሰዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ከገዥው ፓርቲም ከተቃዋሚዎችም ወገን ሳይሆኑ ሁሉንም አካላት በገለልተኛነት የማገልገል ግዴታ እንዳለባቸው በማስረዳት፤ በማንኛውም ጊዜ ለውይይት በራቸው ክፍት መሆኑን አረጋግጠውልናል ብለዋል- የመኢአድ ፕሬዚዳንት፡፡
መኢአድን ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ተቃዋሚ ፓርቲዎች ፕሬዚዳንቱ በአንድ ላይ ሰብስበው በሀገሪቱ ችግሮች ላይ እንዲያወየዩ ጠይቀናል ያሉት ዶ/ር በዛብህ፤ ለጥያቄያችንም አዎንታዊ ምላሽ እንዳላቸው ተገንዝበናል ብለዋል፡፡

Read 11124 times