Saturday, 28 May 2016 15:09

“ሀገሪቱ በዲሞክራሲና በፍትህ ወደፊት አልተራመደችም”

Written by 
Rate this item
(26 votes)

“ሀገሪቱ በዲሞክራሲና በፍትህ ወደፊት አልተራመደችም”


ባለፉት 25 ዓመታት ሀገሪቱ በዲሞክራሲ፣ በሰብአዊ መብትና በፍትህ የሚጠበቅባትን ያህል ወደፊት አልተራመደችም ሲሉ አንጋፋ የህግ ባለሙያዎች የተቹ ሲሆን የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ም/ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፤ በአሁኑ መንግስት ከምንግዜውም የተሻለ የዲሞክራሲ፣ የሰብአዊ መብትና የፍትህ ስርአት ተዘርግቷል ብለዋል፡፡ አንጋፋው የህግ ባለሙያ አቶ አብዱ አሊ ሂጅራ ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ “ዲሞክራሲ ማለት ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት ነው፤ በአሁን ወቅት ግን በኢትዮጵያ ውስጥ የሃሳብ ልዩነትን ማስተናገድ የሚችል ስርአት አልተፈጠረም” ብለዋል፡፡
“ዲሞክራሲ በሌለበት ነፃ ፍ/ቤት ሊኖር አይችልም” ያሉት ዓለምአቀፉ የህግ ባለሙያ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም በበኩላቸው፤ ወንጀል የሰሩ ከፍተኛ ባለስልጣናት በህግ አለመጠየቃቸውን ጠቅሰው የህግ የበላይነትም እየተከበረ አይደለም ብለዋል፡፡ “ለፍትህ ስንቅ የሆኑ አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን የሚንዱ አዋጆች መፅደቃቸው የፍትህ ስርአቱ ወደፊት እንዳይራመድ አድርጎታል” ሲሉም ተችተዋል፤ ዶ/ር ያዕቆብ፡፡
ሌላው የህግ ባለሙያ አቶ ተማም አባቡልጉ፤ የፍትህ ስርአቱ በሚፈለገው መጠን ገና እንዳልተመሰረተ ገልፀው፤ የፍትህ ተቋማት መኖር ብቻውን ፍትህ አለ አያስብልም ብለዋል፡፡
“የህግ የበላይነት ሠፍኗል ብዬ አላምንም” ያሉት አቶ ተማም፤ የሰብአዊ መብት ጥሰት ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ነው ብለዋል፡፡ የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ም/ፕሬዚዳንት አቶ በሪሁ ተ/ብርሃን በበኩላቸው፤ የስርአት ለውጥ ሲመጣ የዳኝነት ነፃነትና ተጠያቂነት ህገመንግስታዊ እንዲሆን መደንገጉ፣ በፍትህ ስርአቱ ላይ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል፡፡
 ዲሞክራሲና ሰብአዊ መብትን የማስፈን ጉዳይ በህግ የበላይነት የሚመራ እንደመሆኑ ፍ/ቤቶች በዚህ በኩል ተገቢውን ተግባር እየተወጡ እንደሆነም ም/ፕሬዚዳንቱ ገልፀዋል፡፡

Read 4078 times