Saturday, 28 May 2016 15:02

የፓትሪያሪኩን ስም በማጥፋት የተከሰሰው የ“ሰንደቅ” ዋና አዘጋጅ በዋስ ተለቀቀ

Written by 
Rate this item
(9 votes)

የ100ሺ ብር የፍትሃብሔር ክስም ቀርቦበታል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክርስቲያን መንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ፅ/ቤት፣ የፓትሪያርኩን ስም በማጥፋት ወንጀል የተከሰሰው የ“ሰንደቅ” ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ፍሬው አበበ ፍ/ቤት ቀርቦ በ5ሺህ ብር ዋስ ተለቀቀ፡፡ ቤተ ክህነት ከወንጀል ክሱ በተጨማሪ ላይ የ100 ሺህ ብር ካሳ እንዲከፈላትም በጋዜጠኛው ላይ የፍትሃ ብሄር ክስ አቅርባለች፡፡
መጋቢት 25 ቀን 2008 ዓ.ም በ“ሰንደቅ” ጋዜጣ ዕትም ላይ “ፓትርያርኩ ለኢትዮጵያ የደህንነት ስጋት ለምዕመናን የድህነት ስጋት” በሚል ርዕስ የተፃፈውን ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ፅሁፍ በማተሙ ነው ቤተ ክህነት ክሱን የመሰረተችው፡፡
ቤተክህነት ያቀረበችው የቀረበው የክስ ዝርዝር እንደሚያስረዳው፤ ለክሱ ምክንያት የሆነው የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ፅሁፍ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋዋማዊ አሰራር ጥላሸት የሚቀባና የፓትርያርኩን ስም የሚያጠፋ እንዲሁም በመልካም ስምና ዝናቸው ላይ ከባድ ጉዳት በማድረስ ህዝበ ክርስቲያኑ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማዊ አሰራር እንዳይቀበል የሚያደርግ ፅሁፍ በጋዜጣው ታትሞ እንዲወጣ ያደረገ በመሆኑ በፈፀመው ስም የማጥፋት ወንጀል መከሰሱን ይጠቁማል፡፡ ቤተ ክህነቷ ከዚሁ የክስ ጭብጥ ጋር በተያያዘ ጋዜጠኛው አድርሶብኛል ላላቸው የህሊና ጉዳት የ100 ሺህ ብር ካሳ የጠየቀችበትን የፍትሃ ብሄር ክስም አቅርባለች፡፡ ጋዜጠኛው ባለፈው ረቡዕ በፌደራል የመጀመሪያ ፍ/ቤት ቂርቆስ ምድብ 2ኛ ወንጀል ችሎት ቀርቦ፤ በስራ መደራረብ ምክንያት ባለሙያ ለማማከር እንዳልቻለ በማስረዳት ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጠው በጠየቀው መሰረት ፍ/ቤቱ ለግንቦት 23 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ለቀረበበት የ100 ሺህ ብር የፍትሃ ብሄር ክስ ክርክር ለግንቦት 26 ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

Read 3585 times