Saturday, 28 May 2016 09:24

ዛምቢያ ለ40 ኢትዮጵያውያን እስረኞች ምህረት አደረገች

Written by 
Rate this item
(3 votes)

554 እስረኞች እንዲለቀቁ ወስኗል
የዛምቢያ ፕሬዚዳንት ኤድጋር ሉንጉ 40 ኢትዮጵያውያን ወጣት ጥፋተኞችን ጨምሮ በተለያዩ ወንጀሎች ተከስሰው ለተቀጡና በእስር ላይ ለሚገኙ 554 እስረኞች ባለፈው ማክሰኞ ምህረት ማድረጋቸውን ዛምቢያን ናሽናል ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዘገበ፡፡ፕሬዚዳንቱ ባለፈው ረቡዕ የተከበረውን የአፍሪካ የነጻነት ቀን ምክንያት በማድረግ ባስተላለፉት የምህረት ውሳኔ፣ ከእስር እንዲፈቱ የተወሰነላቸው ኢትዮጵያውያን ወጣት ጥፋተኞች መቼና በምን ወንጀል ተከስሰው ለእስር እንደተዳረጉ የታወቀ ነገር የለም ያለው ዘገባው፣ ከ2015 አንስቶ ከ100 በላይ ኢትዮጵያውያን በዛምቢያ እንደታሰሩ ጠቁሟል፡፡ምህረት የተደረገላቸው ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ሁሉም በወጣትነት የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ እንደሆኑ የጠቆመው ዘገባው፣ ታስረውበት የነበረው እስር ቤት ግን የአዋቂዎች እንደሆነና፣ መንግስት ባወጣው የምህረት ውሳኔ ኢትዮጵያውያኑን ማካተቱ ትርጉም ያለው ነገር ነው መባሉን ገልጧል፡፡በርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በዛምቢያ ሉዋንጉዋ ድንበር በኩል አድርገው ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሻገር እንደሚሞክሩ የገለጸው ዘገባው፣ የአገሪቱ ፖሊሶችና የኢሚግሬሽን ሰራተኞችም በህገወጥ መንገድ ድንበር የሚያቋርጡ ኢትዮጵያውያን ስደተኞችን እየተከታተሉ በቁጥጥር ስር ማዋል መቀጠላቸውን አስረድቷል፡፡

Read 1795 times