Saturday, 28 May 2016 09:38

ሸገር የከተማ አውቶቡስ ሥራ ጀመረ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

          የአዲስ አበባ ከተማን የትራንስፖርት ችግር እንደሚፈታ የተነገረለት ሸገር የከተማ አውቶቡስ ትናንት ስራ የጀመረ ሲሆን ለአንድ አውቶቡስ 3.61 ሚ. ብር ፣ ለ50 አውቶብሶች 180 ሚ. ብር ወጪ መደረጉ ታውቋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽ/ቤት፣ ብረታ ብረት ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን እንዲሰራለት ካዘዛቸው 300 አውቶቡሶች ውስጥ 50ዎቹን ተረክቦ ሥራ
ማስጀመሩን የአስተዳደሩ የትራንስፖርት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት ካፓሲቲ ኦፕሬሽን መምሪያ ኃላፊ
አቶ ሙሉቀን አማረ ገልጸዋል፡፡ አውቶብሶቹ ከአንድ ኪሎ ሜትር በታች የሚቆሙ ስላልሆነ፣ የረዥም ርቀት ፍላጎት የሚያሟሉ ናቸው ያሉት አቶ ሙሉቀን፤ ታሪፋቸውም ኪስ አይጎዳውም ብለዋል፡፡ እስከ 4 ኪሎ ሜትር 1.50፣ ከ4-6 ኪ.ሜ 2 ብር፣ ከ6-9 ኪ.ሜ 3 ብር፣ እስከ 10 ኪሎ ሜትር ርቀት 3.50 እንደሚያስከፍሉ በመግለፅ፡፡ አውቶብሶቹ ለጊዜው የሚጓዙባቸውና የተመረጡ መስመሮች፡- ከሜክሲኮ ቦሌ፣ ከቦሌ ፒያሳ፣ ከፒያሳ መገናኛ፣ ከሜክሲኮ ዓለም ባንክ፣ ከሳሪስ አቦ መገናኛ እንደሆኑ የጠቀሱት ኃላፊው፤ ከ3ወር በኋላ 150 አውቶብሶች ሲረከቡ የመስመሮቹ ቁጥር 21 እንደሚደርስና የቀሩትን አውቶቡሶች አጠናቀው አጠናቀቁ ሲረከቡ እንደየአስፈላጊነቱ ሌሎች መስመሮች እንደሚከፈቱ አስረድተዋል፡፡ ሸገር አውቶቡስ የተቋቋመበት ሦስት መሰረታዊ ነገሮች አሉት ያሉት ኃላፊው፣ በአንድ ኪ.ሜ የሚቆም መደበኛ አገልግሎት፣ የተማሪዎች የትራንስፖርት አገልግሎትና ፈጣን የትራንስፖርት
አገልግሎት (ከአስኮ እስከ ጀሞ (16 ኪ.ሜ) እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ሸገር አውቶቡስና አንበሳ አውቶቡስ ሁለቱም የመንግስት የልማት ድርጅቶች ስለሆኑ ጎን ለጎን ይሰራሉ ያሉት አቶ ሙሉቀን፤ አንበሳ አውቶቡስ 814 አውቶቡሶች፣ ሲቪል ሰርቪስ ወደ 400 አውቶቡሶች፣ ሸገር ደግሞ 300 አውቶቡሶች ይኖሩታል፣ ሆኖም ጥናቶች፤ የከተማዋ የትራንስፖርት ፍላጎት በአማካይ 3500 አውቶቡሶች እንደሆነ የሚያመለክቱ ስለሆነ ሌሎች ተጨማሪ አውቶቡሶች ያስፈልጋሉ ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት አውቶቡስ ለመጠበቅ ከአንድ ሰዓት በላይ መጠበቅ ያስፈልጋል ያሉት ኃላፊው፤ የሸገር አውቶቡሶችን በ10 ደቂቃ ውስጥ ማግኘት እንደሚቻል ቢገልፁም በምን መንገድ እንደሆነ አልገለፁም፡፡ የሸገር ዘመናዊ አውቶቡሶች የደህንነት ካሜራ የተገጠመላቸው ሲሆን፣ አውቶብሶቹ የት እንዳሉ መቆጣጠር የሚያስችል ጂፒኤስ፣ የአየር መቆጣጠሪያ ኤሲ እንዳላቸውና፣ አውቶማቲክ ትኬት እንደሚጠቀሙ ሃላፊው ተናግረዋል፡፡

Read 3077 times