Saturday, 14 May 2016 11:54

ኢትዮጵያዊው ወጣት በደቡብ አፍሪካ ዘራፊዎች ተገደለ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

       በደቡብ አፍሪካ ምስራቃዊ ኬፕታውን በሚገኘው ሴንት ፍራንሲስ ቤይ የተባለ አካባቢ በንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ የሚኖር አንድ ኢትዮጵያዊ ባለፈው ሳምንት በዘራፊዎች መገደሉንና ይህን ተከትሎ በአካባቢው የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎች መደብሮች በአገሬው በመዘረፍ ላይ እንደሚገኙ ተዘገበ፡፡
ኢዮብ ማዴሞ የተባለው ኢትዮጵያዊ የ27 አመት ወጣት ከ9 ቀናት በፊት ክዋኖምዛሞ በተባለው አካባቢ በሚገኘው መደብሩ ውስጥ እያለ በአንድ ዘራፊ መገደሉን ያስታወሰው ዘገባው፣ ወጣቱን በመግደል የተጠረጠረው ዘራፊ የሌላን ኢትዮጵያዊ መደብር ዘርፎ ካመለጠ በኋላ፣ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያውያን ናቸው በተባሉ የአካባቢው ነዋሪዎች በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ማለፉን ገልጧል፡፡
ይህም በአካባቢው በሚገኙ ደቡብ አፍሪካውያን ላይ ቁጣ መቀስቀሱንና የተደራጁ ዘራፊዎች ሲ ቪስታ በተባለው አካባቢ የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎችን መደብሮች መዝረፍ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የአካባቢው የፖሊስ ቃል አቀባይም ስምንት ያህል የውጭ አገራት መደብሮች መዘረፋቸውን እንዳረጋገጡ ገልጧል፡፡
ፖሊስ ዝርፊያውን ለማስቆም በአካባቢው መሰማራቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በዘረፋው ላይ ተሰማርተዋል በሚል የተጠረጠሩ ሶስት ደቡብ አፍሪካውያንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ከትናንት በስቲያ በሁማንስ ድሮፕ ፍርድ ቤት መቅረባቸውን አስታውቋል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ የሉዋንግዋ ፍርድ ቤት በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ወደ ዛምቢያ ገብተዋል በሚል በተከሰሱ 41 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ሉሳካ ታይምስ የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘግቧል፡፡ በቀረበባቸው ክስ ጥፋተኛ ሆነው የተገኙት ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች፤ የገንዘብ ወይም የሶስት ወራት እስር እንደሚጠብቃቸው የገለጸው ዘገባው፣ ስደተኞች ዕድሜያቸው ከ30 አመት በታች መሆኑን አስታውቋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች ሉዋንግዋ ተብሎ በሚጠራው የድንበር አካባቢ አቋርጠው ወደ ዚምባቡዌ ሊያመሩ ሲሉ በዛምቢያ ፖሊስና የደህንነት አካላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ተነግሯል፡፡
ባለፈው ወርም በተመሳሳይ ሁኔታ ይህን ድንበር ለማቋረጥ የሞከሩ 16 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በአገሪቱ የደህንነት ሃይሎች በቁጥጥር ስር እንደዋሉም ዘገባው አስታውሷል፡፡

Read 4603 times