Saturday, 07 May 2016 13:42

ሼክ አላሙዲ ለመቄዶኒያ 16 ሚ. ብር ለገሱ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ሼክ መሀመድ አሊ አላሙዲ ለመቄዶኒያ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ 16 ሚ. ብር ለገሱ፡፡ እርዳታውን ለማዕከሉ ያስረከቡት የሞሀ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ስራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ሲሆኑ የተረከቡት ደግሞ የማዕከሉ መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቢኒያም በለጠ እንደሆኑ ታውቋል፡፡
ከርክክብ ስነስርዓቱ በኋላ የመቄዶኒያ መስራች አቶ ቢኒያም በለጠ ባደረጉት ንግግር፤ ሼክ አሊ አላሙዲ ከዚህ ቀደም እንደነ ደርባ ሲሚንቶ፣ ኒያላ ሞተርስ፣ የላይኛው አዋሽ አግሮ ኢንዱስትሪ፣ አዲስ ፓርክ፣ አዲስ ጐማ፣ ኤልፎራ፣ ኩዊንስ ሱፐር ማርኬትና ሚድሮክ አንሊሚትድ ፓኪንግ ፋክተሪ በመሳሰሉ ድርጅቶቻቸው በኩል ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ መለገሳቸውን አስታውሰው፤ በሼኩ የተለገሱት አምቡላንሶችም ከ800 በላይ ተጨማሪ እርዳታ የሚፈልጉ ደካሞችን ከየጐዳናው ለማንሳት እንዳገዟቸው ተናግረዋል፡፡
አቶ ቢኒያም አክለውም መቄዶኒያ በአሁኑ ወቅት በማዕከሉ ከአንድ ሺህ በላይ አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማንን እየረዳ መሆኑን ጠቅሰው ለዕለት ፍጆታ ብቻ በየወሩ ከ1ሚ. ብር እንደሚያወጣ ገልፀዋል። ከ300 ሚ.ብር በላይ ለሚያስፈልገው ማዕከል ግንባታ ማህበረሰቡ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አድንቀው ድጋፉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የተማፀኑት መስራቹ፤ ሼክ አላሙዲ የለገሱት 16 ሚ. ብርም ለማዕከሉ ግንባታ እንደሚውል ተናግረዋል፡፡
የሞሃ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ባደረጉት ንግግርም፤ መቄዶኒያ እያከናወነ የሚገኘውን በጐ ተግባር አላሙዲን እንደሚያደንቁ ገልፀው ወደፊትም እርዳታቸው ከማዕከሉ እንደማይለይ ጠቁመዋል፡፡

Read 2698 times