Saturday, 30 April 2016 11:18

የዘንድሮ የትንሳኤ በአል ገበያ ምን ይመስላል?

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(12 votes)

    በተለያዩ የአዲስ አበባ የገበያ ስፍራዎች ተዟዙረን የበዓል ገበያ ዋጋን ለመቃኘት እንደሞከርነው፤ በአብዛኛው ከዓምና ተመሳሳይ የበዓል ገበያ ዋጋ ጋር ተቀራራቢ ነው፡፡ በአቃቂ ቄራ ገበያ የበሬ ዋጋ ከ5 ሺህ እስከ 22 ሺህ ብር ድረስ ሲሆን ዓምና በተመሳሳይ በዓል የበሬ ዋጋ ከ8 ሺህ ብር እስከ 25 ሺህ እንደነበረ ይታወሳል፡፡
በአቃቂ ቄራ፡- የበግ ዋጋ ከ700 ብር እስከ 3500 ብር ሲሆን በዓምና የፋሲካ ገበያም በግ ከ900ብር እስከ 3500 ብር ተሸምቷል፡፡ በአቃቂ የቁም እንስሳት ቄራ ገበያ፣ ከፍተኛው የፍየል ዋጋ 7ሺህ ብር መሆኑን ከነጋዴዎች የተገኘው መረጃ አመልክቷል፡፡
በገበያው ቋሚ የበግና የፍየል ነጋዴ የሆነው ወጣት መስፍን ይልማ፤ በግና ፍየሎችን ከአዳማና አርሲ አካባቢ አምጥቶ እንደሚሸጥ ገልፆ፤ ዘንድሮ ገበሬው በግና ፍየል ለነጋዴው እየሸጠበት ያለው ዋጋ ከአምናው ጋር ሲነፃፀር በአማካይ እስከ 200 ብር ቅናሽ ማሳየቱን ተናግሯል፡፡
ገበሬው ለመጪው ክረምት የሰብል ምርት የሚያስፈልገውን ማዳበሪያ መግዣ የሚሆን ገንዘብ ለማግኘት የትንሳኤ በዓል የከብት ገበያን እንደመልካም አጋጣሚ እንደሚጠቀምበት ይኸው ነጋዴ ገልጿል፡፡
በአዲስ አበባ ዋናው ቄራ ገበያ የሃረር ሰንጋ በሬዎች፡- ከ18 ሺህ ብር እስከ 25 ሺህ ብር እየተሸጡ ሲሆን በሰውነት አቋማቸው አጫጭር የሆኑት የጅማ ሰንጋዎች ደግሞ ከ6 ሺህ ብር እስከ 10ሺህ ብር እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ በግ በቄራ አካባቢ ባሉ ገበያዎች መካከለኛው፡- ከ1300 ብር እስከ 2ሺህ ብር፣ ሙክት በግ እስከ 5 ሺህ ብር ይገኛል፡፡
የዶሮ ዋጋ ዝቅተኛው 130 ብር፣ ከፍተኛው 400 ብር ሲሆን እንቁላል በነጠላ 3 ከ50፣ ቅቤ በኪሎ፣ ከ180 ብር እስከ 240 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ በአስኮ ገበያ ዶሮ ከ250 ብር እስከ 350 ብር፣ እንቁላል በነጠላ 3 ብር 50፣ ቅቤ በኪሎ ከ180 ብር እስከ 250 ብር፣ አይብ ከ65-75 ብር በኪሎ ይሸጣል፡፡
 የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅት በበኩሉ፤ 5ሺህ የሚሆኑ የእርድ እንስሳትን የሚያቀርብ ሲሆን ከነዚህም ውስጥ 2500 በሬዎች፣ 2300 ደግሞ በግና ፍየሎች እንደሆኑ ገልጿል፡፡ ከድርጅቱ ባገኘነው መረጃ መሰረት፤ ለበዓሉ ድርጅቱ በራሱ የመሸጫ ሱቅ የበግ ስጋ በኪሎ 130 ብር ይሸጣል፡፡

Read 5631 times