Saturday, 16 April 2016 12:37

በጆሐንስበርግ መድኃኔዓለም የተፈጠረ ውዝግብ ምዕመናንን ለዐምባጓሮ አደረሰ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(30 votes)

-    አምስት ምእመናን ለእስር ተዳርገዋል
-    የውጭ ጉዳይ ሓላፊው ተጠያቂ ተደርገዋል
-    ሰበካ ጉባኤው በፕሪቶርያ ፍ/ቤት ክሥ መሥርቷል
አለማየሁ አንበሴ
በደቡብ አፍሪካ ጆሐንስበርግ ጽርሐ ጽዮን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአስተዳደር ሳቢያ የተፈጠረ አለመግባት ወደ ዐምባጓሮ አምርቶ 8 ምእመናን የተጎዱ ሲሆን ጉዳዩም በሀገሪቱ ፍ/ቤት መያዙ ተገለጸ፡፡
በቤተ ክርስቲያኒቱ ሰበካ ጉባኤ እና በቅርቡ በቤተ ክርስቲያኒቷ አስተዳዳሪነት በተሾሙት አባ ጥዑመ ልሳን አዳነ መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ያስከተለው ግጭት ለስምንቱ ምእመናን መጎዳት ምክንያት መሆኑን ምንጮቹ ጠቅሰዋል፤ አንዲት የአራት ወራት ነፍሰ ጡርም በዐምባጓሮው ወቅት ወድቃ በመረገጧ ክፉኛ ተጎድታ በሕክምና ላይ እንደምትገኝ ተናግረዋል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን የውጭ ጉዳይ መምሪያ ሓላፊን ጨምሮ ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት ያሉበት አጣሪ ኮሚቴ በቋሚ ሲኖዶስ ተልኮ እንደነበር ያስታወሱት ምንጮቹ፤ ይሁንና የኮሚቴው አባላት በአቋም መከፋፈላቸውንና የተለያየ ሪፖርት ለሲኖዶሱ ማቅረባቸውን እንደሰሙ ገልጸዋል፤ “ለሽምግልና የተላከ ሰው እንዴት አጣልቶ ይመለሳል?” ሲሉ የሚጠይቁት ምንጮቹ የአጣሪው ኮሚቴ አባል የሆኑትን የመምሪያ ሓላፊ ለቋሚ ሲኖዲሱ የተዛባ ሪፖርት በማቅረብ ይወቅሷቸዋል፤ ለግጭቱ መባባስም “ዋነኛ ተጠያቂ ናቸው፤” ብለዋል፡፡
 
የግጭቱ መንሥኤ አስተዳዳሪው አባ ጥዑመ ልሳን በተጭበረበረ ሰነድና ቤተ ክርስቲያኗ በሌላት የሥልጣነ ክህነት ተዋረድ (Deputy Bishop) ተብለው የደቡብ አፍሪካ ሀገረ ስብከትና የደብሩ አስተዳደር ሆነው ተሹመዋል፤ የሚል ቅሬታ መሆኑን ከስፍራው ለአዲስ አድማስ የደረሱ መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡
አባ ጥዑመ ልሳን ቀደም ሲል ደብሩን ለሁለት ዓመት ካገለገሉ በኋላ በገዛ ፈቃዳቸው ከኃላፊነታቸው በመልቀቅ ወደ ሀገር ቤት ተመልሰው ነበር፤ የሚሉት የሰበካ ጉባኤው አመራሮች፤ የደቡብ አፍሪካን የሥራ ፈቃድ ሳያሟሉ በጎብኚ ቪዛ በመግባት ከፓትርያርኩ ሹመት ተሰጥቶኛል በማለት የአስተዳዳሪነቱን ቦታ መልሰው መያዛቸውን አስረድተዋል፡፡
ይህም በሰበካ ጉባኤው ዘንድ ከፍተኛ ቅሬታ በመፍጠሩ ለደቡብ አፍሪካ የሀገር ውስጥ ሚኒስቴር (ኦማሬር ሚኒስቴር) ተደጋጋሚ ቅሬታ ማቅረባቸውን የሰበካ ጉባኤው ም/ሰብሳቢ አቶ ዳዊት ሰሎሞን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤትም አቤቱታ ማቅረባቸውን የጠቀሱት አቶ ዳዊት፤ የቅዱስ ሲኖዶሱን ምላሽ እየተጠባበቅን ባለበት “አባ ጥዑመልሳን ከፓትሪያርክ አባ ማትያስ የሰበካ ጉባኤውን የሚያግድ ደብዳቤ ተልኮልኛል፤ በማለት በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰበው ምእመን ሊያነቡ ሲሉ ዐምባጓሮ መፈጠሩን አስታውቀዋል፡፡
ግጭቱን ተከትሎ የሰበካ ጉባኤው ለፕሪቶሪያ ሠራተኛ ፍ/ቤት ክሥ ያቀረበ ሲሆን፣ የአስተዳዳሪውን የአባ ጥዑመ ልሳንን ጨምሮ በርካታ ቅሬታዎች እየቀረቡለት ጉዳዩን በቸልታ ተመልክቷል የተባለው የሀገሪቱ የኦማሬር ሚኒስቴር በክሡ ተካቷል፡፡
ሚኒስቴሩ ለፍ/ቤቱ በሰጠው ምላሽ፣ የተጠቀሱበትን ክሦች እንደሚቀበልና ለጉዳዩ አፅንዖት ሰጥቶ የማስተካከያ ርምጃ እንደሚወስድና ለአስተዳዳሪው የሰጠውን ፈቃድ እንደሚሰርዝ ማሳወቁን የጠቀሱት የሰበካ ጉባኤው የሕዝብ ግንኙነት ተጠሪ አቶ ይልማሸዋ፤ አባ ጥዑመ ልሳንም ለክሡ መልስ አቀርባለሁ ማለታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ክሡ በዚህ ደረጃ ላይ እያለ “ሰበካ ጉባኤው ታግዷል” መባሉ ውዝግቡን እንዳባባሰው አቶ ይልማ ሸዋ አክለው ገልጸዋል፡፡
ደቡብ አፍሪካውያን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን፤ “የጥቁሮች ቤተ ክርስቲያን”፤ “የአፍሪካ ቤተ ክርስቲያን”፤ “የኛ ቤተ ክርስቲያን” እንጂ የስደተኞች ቤተ ክርስቲያን አድርገው እንደማያዩዋት ያስረዱት ምእመናኑ፣ በዐምባጓሮው ሳቢያ ግን ህፃናት ወደ ደብሩ ለመምጣት ስጋት እንዳደረባቸው ተናግረዋል፤ የሀገሪቱ ቴሌቪዥንም ግጭቱን ጨምሮ ለውዝግቡ ሽፋን ሊሰጠው መዘጋጀቱን ጠቁመዋል፡፡

Read 6537 times