Saturday, 25 February 2012 13:35

የኦስካር ስነስርዓት ነገ ይካሄዳል

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

84ኛው የኦስካር ሽልማት ስነስርዓት ነገ ሌሊት ሎስአንጀለስ በሚገኘው የኮዳክ ትያትር ሲካሄድ በኤቢሲ ቻናል የቀጥታ ስርጭት እስከ 40 ሚሊዮን ታዳሚ እንደሚያገኝ ተገምቷል፡፡ በምርጥ ፊልም ፤ በምርጥ ወንድና ሴት ተዋናዮችና በምርጥ ዲያሬክተሮች ምርጫ የሚያሸንፉትን ለመገመት አስቸግሯል፡፡ በ11 ዘርፎች ታጭቶ ከአንድ በላይ ሽልማቶችን ለመሰብሰብ  ከፍተኛውን እድል የያዘው ‹ሁጎ› እና አስቀድሞ በርካታ ሽልማቶችን የሰበሰበው  በ10 ዘርፎች የታጨው “ዘ አርቲስት” ፉክክር ከፍተኛ ትኩረት ስቧል፡፡

የኦስካር አሸናፊዎችን በመምረጥ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያላቸው የአካዳሚ ኦፍ ሞሽን ፒክቸርስ አባላት ተዋፅኦ ለጥቁሮችና ለሴቶች በቂ ቦታ አልሰጠም በሚል የሽልማት ስነስርዓቱ ተብጠልጥሏል፡፡  ከ5783 የአካዳሚው አባላት 94 በመቶ ነጮች እንዲሁም 77 በመቶ ያህሉ ወንዶች መሆናቸውን ሎስ አንጀለስ ታይምስ ይፋ ባደረገው የምርመራ ሪፖርት አረጋግጧል፡፡ ከኦስካር ምሽት በኋላ በታዋቂ ሰዎች የተዘጋጁ የፓርቲ ድግሶች አሸናፊዎችን በእንግድነት ለመጋበዝ ሽሚያ ገብተዋል፡፡ከኦስካር ምሽቱ በኋላ ብዙዎቹ አሸናፊዎች ይታደሙታል የተባለው ፓርቲ “ጋቨርነርስ ቦል” የተባለው ሲሆን በፓርቲው 1500 እንግዶች 1000 ጠርሙስ ምርጥ ሻምፓኝ ይራጫሉ ተብሏል፡፡ ከፓርቲዎቹ መካከል ማዶና እና ዴሚ በጋራ ያዘጋጁት እና የኤልተን ጆን የኤድስ ፋውንዴሽን ያሰናዳው ተጠቃሽ ናቸው፡፡ 84ኛው ኦስካር እስከ 80 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኛል ተብሎ ሲጠበቅ  የአምናው ስነስርዓት  74.4 ሚሊዮን ዶላር አስገኝቷል፡፡

 

 

Read 1141 times Last modified on Saturday, 25 February 2012 13:37