Saturday, 26 March 2016 10:24

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እገዳ በፓትርያርኩ ትእዛዝ ተነሳ

Written by 
Rate this item
(5 votes)

     የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ ለልጃቸው ሕክምና
የገንዘብ ርዳታ የወሰኑላቸውን የእንጦጦ ኪዳነ ምሕረት ገዳም 10 የአስተዳደር ኮሚቴ አባላትን
ከሥራና ከደሞዝ ያገዱ ቢሆንም ፓትርያርኩ እግዱን ሽረውታል፡፡ ሥራ አስኪያጁ፣ “ለታማሚ ልጃቸው ማሳከሚያ” በሚል ገንዘብ በማሠባሰብ ላይ እንደነበሩ መዘገቡ የሚታወስ ሲሆን፤ ከእንጦጦ ኪዳነ ምህረት ገዳም ብቻ ግማሽ ሚሊዮን ብር በገዳሙ አስተዳደር ኮሚቴ እንዲሰጣቸው ቢወስንም፤ የገዳሙ ሒሳብ ሹም ክፍያውን አልፈጽምም በማለታቸው ውዝግብ ተፈጥሮ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ከትላንት በስቲያ በሥራ አስኪያጁ  እግድ ተላልፎባቸው ከነበሩት የአስተዳደር ኮሚቴ አባላት አንዱ፣ ሥራ አስኪያጁ በፅ/ቤታቸው ጠርተዋቸው ሁሉንም የአስተዳደር አካላት “ስሜን ለማስጠፋት ሆን ብላችሁ ሳላዛችሁ የሰራችሁት ነው፤” በሚል ቃለ ጉባኤውን በቃለ ጉባኤ ካልሻራችሁ፤” በሚል ሁሉንም ማገዳቸውን እንዳሳወቋቸው ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡ “ሥራ አስኪያጁ እገዳውን ካስተላለፉብን በኋላ የታገድንበትን ደብዳቤና የገንዘብ ርዳታውን የወሰንበትን ቃለ ጉባኤ ይዘን ቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በመግባት አስረዳናቸው፤” ያሉት የአስተዳደር ኮሚቴው አባላት፤ በሌሎች አድባራትና ገዳማት እንደተደረገው ሁሉ እርዳታውን የሰጡት ለዚሁ ዓላማ ተዋቅሮ በተላከ ኮሚቴ በተጠየቁት መሠረት መሆኑን ለፓትርያርኩ ማሳወቃቸውን
ገልጸዋል፡፡ አቤቱታውን ያዳመጡት ፓትርያርኩ፤ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅና የገንዘብ ርዳታ የወሰኑትን አቤቱታ አቅራቢዎች ገሥጸው፣ የሥራ አስኪያጁን እገዳ በማንሳት የገዳሙ የአስተዳደር ኮሚቴ
አባላት ወደ መደበኛ ሥራቸው እንዲመለሱ ለሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በላኩት ደብዳቤ ማዘዛቸው
ታውቋል፡፡  

Read 2885 times