Saturday, 23 January 2016 13:24

የኢትዮ - ሱዳን ድንበር ማካለል ዳግም እያነጋገረ ነው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(20 votes)

“ድንበሩን ለማካለል በዚህ አመት የተያዘ ምንም አይነት እቅድ የለም” - የኢትዮጵያ መንግስት
“በዚህ አመት የድንበር ማካለሉ ይጠናቀቃል” - የሱዳን መንግስት

      የሱዳን መንግስት ባለስልጣናት የኢትዮ ሱዳን የድንበር ማካለል በዚህ ዓመት ይጠናቀቃል ሲሉ የሰጡትን መግለጫ የኢትዮጵያ መንግስት እንደማያውቀው ገልፆ በዚህ አመት የተያዘ ምንም ዓይነት ድንበር የማካለል ዕቅድ እንደሌለ አስታወቀ፡፡
በዚህ አመት በሁለቱ ሀገራት መካከል የድንበር ማካለል እቅድ እንደሌለ የኢትዮጵያ መንግስት በተደጋጋሚ መግለፁን የጠቆመው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት፤ አሁንም የተለወጠ ነገር አለመኖሩን ለአዲስ አድማስ አመልክቷል፡፡
በድንበሩ ጉዳይ በኢትዮጵያ በኩል እየተደረገ ያለ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንደሌለ ያስታወቁት የመንግስት ኮሙኒኬሽን የሚዲያ ግንኙነት ሃላፊ አቶ መሐመድ፤ “የሱዳን ጋዜጦችና አንዳንድ የሱዳን መንግስት ሃላፊዎች የፈለጉትን ነገር ሊገልፁ ይችላሉ፤ ነገር ግን ኢትዮጵያ ምንም የያዘችው እቅድ የለም ሲሉ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡
መቀመጫውን ካርቱም ያደረገው “ሱዳን ትሪቡን” ጋዜጣ፤ የኢትዮ ሱዳን የድንበር ጉዳይ ቴክኒክ ኮሚቴ፣ በዚህ አመት የሃገራቱ ድንበር ተካሎ ይጠናቀቃል ሲል ዘግቧል፡፡
በጥቅምት 2014 እ.ኤ.አ የሱዳኑ ፕሬዚዳንት አል በሽርና የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም ደሣለኝ፤ የድንበር ማካለሉ እንዲከናወን ውይይት ማድረጋቸውን ሱዳን ትሪቡን   አስታውሷል፡፡
የድንበር ጉዳዩ ቴክኒካል ኮሚቴ ሰብሳቢ አብደላ አል ሣዲግ፤ የድንበር ማካለሉ ሂደት ምንም ችግር እንዳላጋጠመው ለጋዜጣው ጠቁመው፤ 725 ኪ.ሜትር የሚረዝመውን የሁለቱን ሀገራት ድንበር የማካለል ጉዳይ በተሳካ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በደቡብ ምስራቅ ሱዳን ገዳሪፍ ግዛት ውስጥ ይገኛል የሚባለው 250 ስኩዬር ኪ.ሜትር የሚያካልለው የአል ፋሽጋ አካባቢ በአሁን ወቅት የሱዳንና የኢትዮጵያ ገበሬዎች ሰብል የሚያመርቱበት መሆኑን የጠቀሰው “ሱዳን ትሪቡን” ዋነኛ የውዝግብ ቦታ መሆኑንም አመልክቷል፡፡
አል ፋሽጋ የተባለው ይህ አካባቢ፤ 600.000 ሄክታር ለም መሬት ያለው ሲሆን አትባራ፣ ሰታይት እና ባሰላም የተባሉ ወንዞች የሚፈስቡት በመሆኑ ለመስኖ እጅግ ተመራጭ ቦታ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ይህ ለም መሬት ያለበት አካባቢ የሱዳን ግዛት ነው ያሉት የሱዳኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢብራሂም ጋሃንዶር፣ “ኢትዮጵያም ብትሆን የሱዳን ግዛት ስለመሆኑ ማረጋገጫ ሰጥታለች” ብለዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የሱዳንና የኢትዮጵያ መንግስት በቦታው ላይ ዘልቀው የገቡ የኢትዮጵያ ወንበዴዎችን ለማስወጣት በጋራ እየሰሩ መሆኑን ለአልጀዚራ ገልፀዋል፡፡

Read 8761 times