Saturday, 18 February 2012 10:31

የአዲስ አበባ 125ኛ ዓመት አከባበር ዛሬ በይፋ ይጀመራል

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(0 votes)

“ሥር ነቀል የፖለቲካና የኢኮኖሚ ለውጥ የሚያመጡ ዕቀዶችን ይዘናል”

የከተማዋ ምክትል ከንቲባና የአቅም ግንባታ ቢሮ ኃላፊ ከሃያ በላይ እህት ከተሞች በበዓሉ ላይ ይሣተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡

ህዳር 14/1879 እንደተቆረቆረች የሚነገርላት የአዲስ አበባ ከተማ 125ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ዛሬ በይፋ መከበር ይጀምራል፡፡ በዓሉ እስከመጪው ዓመት ህዳር ወር ድረስ እየተከበረ እንደሚቆይም አቶ አባተ ስጦታው የከተማዋ ምክትል ከንቲባና የአቅም ግንባታ ቢሮ ኃላፊ ገልፀዋል፡፡ “ለአዲስ ለውጥ በአዲስ መንፈስ” በሚል መሪ ቃል ለቀጣዮቹ ዘጠኝ ወራት በተለያዩ ፕሮግራሞች እንደሚከበር የተገለፀው የአዲስ አበባ ከተማ 125ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ ለመታደም ከሃያ በላይ የእህት ከተሞች ከንቲቦች እንደሚገኙና ከተማዋ የአፍሪካ መዲና እንደመሆንዋ መጠን በዓሉ አፍሪካዊ ይዘት እንዲኖረው በማድረግ እንደሚከበር ኃላፊው ገልፀዋል፡፡

በከተማዋ የተንሰራፋውን የመልካም አስተዳደር እጦትና የኑሮ ውድነቱን በተመለከተ ምን ማሻሻያ ሊደረግ ታስቧል ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሰፋ ያለ ምላሽ ከመስጠት የተቆጠቡት ምክትል ከንቲባው፤ በጥቅሉ ሥራ ነቀል የፖለቲካና የኢኮኖሚ ለውጥ የሚያመጡ ዕዶችን ይዘናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በዚህ ዓመት ብቻ ከ100ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጐችን በጥቃቅንና አነስተኛ ለማደራጀት የተያዘው ዕቅድ ከኢኮኖሚ ዕቅዶቹ ውስጥ ተጠቃሽ እንደሆነም ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡

በቅርቡ ተጀመረ ባሉት የ42ሺ ቤቶች ግንባታ ከ210ሺ በላይ የከተማዋ ነዋሪዎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑና በዚህም ከ50ሺ የሚበልጡ ዜጐች የሥራ ዕድል እንዲያገኙ መደረጉ ከተማዋ እያካሄደችው ያለውን የኢኮኖሚ ዕድገት አመላካች ነው ብለዋል፡፡ እስከመጪው ህዳር ወር ድረስ ይዘልቃል በተባለው በዚህ የምስረታ በዓል አከባበር ፕሮግራም ላይ አውደርዕዮች፣ የፓናል ውይይቶች፣ የኪነጥበብ ዝግጅቶች፣ ዶክመንትሪ  ፊልሞች ለእይታ እንደሚቀርቡና የተለያዩ የጉብኝት ፕሮግራሞችም እንደተዘጋጁ ምክትል ከንቲባው ተናግረዋል፡፡

ዛሬ በይፋ በሚጀመረው በዚሁ በዓል የመክፈቻ ሥነ ስርዓት ላይ ከ1200 በላይ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትና የሥራ ኃላፊዎች እንደሚገኙና በመክፈቻ በዓሉም የምስረታውን በዓል አርማ /ሎጐ/ የማስተዋወቅ፣ የከተማዋ ድረ ገፅ/ዌብሳይት ምረቃ ሥነ ስርዓትና ለበዓሉ የተዘጋጀውን መዝሙር ይፋ የማድረግ ፕሮግራም መዘጋጀቱን አቶ አባተ ጨምረው ገልፀዋል፡፡

 

 

Read 2697 times Last modified on Saturday, 18 February 2012 10:34