Saturday, 28 November 2015 14:15

በአበሻ አረቄ አከርካሪውን የተመታው ወረርሽኝ!

Written by  ከሣህሉ ዓለማየሁ (ኢንጂነር)
Rate this item
(9 votes)

   እ.ኤ.አ በ1918 እና 1919 ዓ.ም ስፓኒሽ ፍሉ (የህዳር በሽታ) የተባለ ወረርሽኝ በሽታ ዓለምን ባተራመሰበትና 1/3ኛውን የአውሮፓ ህዝብ በፈጀበት ዘመን፣ በኢትዮጵያም ሰው በተቀመጠበትና በተኛበት ሞቶ በሚቀርበት፣ ሰው ሞቶ ቀባሪ አጥቶ ጅብ የሰው ስጋ አማርጦ መብላት በሰለቸበት በዚያ ክፉ ዘመን፣ ኢትዮጵያዊቷ የባህል መድኃኒት አዋቂ (የአበሻ ዶክተር) መንዜዋ ወ/ሮ ዘነበች፣ ወደ አዲስ አበባ ከተማ መጥተው፣ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ፤ “የአገሬ ህዝብ ሆይ! ከዚህ አስከፊ ወረርሽኝ በሽታ ለመዳን ከፈለግህ፣ የአበሻ አረቄ (ካቲካላ) ጠጣበት፤ ቀይ ሽንኩርት ልጠህ በክር አስረህ፣ በቤት በርና መስኮት ላይ አንጠልጥል” በማለት አዋጅ አስነገሩ። ይህንን የወ/ሮ ዘነበችን አዋጅ የሰማ የፈረንሳይ ቆንስላ ተደናግጦና ተቆጥቶ፣ “አረቄ (አልኮል) መጠጣት በሽታውን ያባብሳልና አልኮል መጠጣት ክልክል ነው” እያለ በከተማው ውስጥ በየቦታው እየተዘዋወረ የበኩሉን አዋጅ አስነገረ፡፡ ነገር ግን የፈረንሳዩ ቆንስላ ያስነገረውን አዋጅ የሰማው እንጂ ከቁም ነገር የቆጠረው ኢትዮጵያዊ ባለመኖሩ ማሳሰቢያው ተቀባይነት አጣ፡፡
በመሆኑም የኢትዮጵያ ሕዝብ የፈረንሳይ ቆንስላውን (የፈረንጁን) ምክር ትቶ የአገሩን ተወላጅ የአበሻ ዶክተሯን የወ/ሮ ዘነበችን ምክር ተቀብሎ የታመመው ለመዳን፣ ያልታመመው ደግሞ በበሽታው ላለመያዝ ሲል ሕፃናት ሳይቀሩ የአበሻ አረቄ እንዲጠጡ ተደረገ፡፡ ቀይ ሽንኩርቱንም እየላጠ በክር አድርጐ ቤቱ ውስጥ አንጠለጠለ። እንደተባለውም በሚያስገርም ሁኔታ በበሽታው ከተያዘ ወዲያውኑ ይሞት የነበረ ሕመምተኛ፣ የአበሻ አረቄውን ሲጠጣ መሞቱ ቀረና ቆይቶ አገግሞ መዳን ጀመረ፡፡ በበሽታው ያልተያዘውም (ያልታመመውም) የአበሻ አረቄውን ሲጠጣ በበሽታው መያዙ ቀረ። መድኃኒቱ ጠፍቶ ዓለምን ያንቀጠቀጠውና ዓለምን የቀጠቀጠው ስፓኒሽ ፍሉ (ሕዳር በሽታ)፤ ለመጀመሪያ ጊዜ በአበሻ አረቄ በኢትዮጵያ ላይ በኢትዮጵያዊቷ የባህል መድኃኒት አዋቂ በአበሻዋ ዶክተር ወ/ሮ ዘነበች አከርካሪውን ተመታ፡፡ ቀደም ሲል አረቄ (አልኮል) መጠጣት ክልክል ነው እያለ አዋጅ ያስነግርና ይለፍፍ የነበረው የፈረንሳይ ቆንስላ፣ መድኃኒቱ በኢትዮጵያ ውስጥ መገኘቱን በመግለጽ፣ ወደ አውሮፓ የደስታ መግለጫ ላከ፡፡ የፈረንሳይ ቆንስላ የደስታ መግለጫ ላከ፡፡ የፈረንሳይ ቆንስላ የደስታ መግለጫውን ብቻ ሳይሆን የአበሻ አረቄና የኢትዮጵያ (የአበሻ) ቀይ ሽንኩርት በገፍ እየገዛ ወደ አውሮፓ መላክ ጀመረ፡፡
የአበሻ አረቄ በአገር ውስጥም ሆነ በውጪ አገር በጣም ተፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ በወቅቱ 10 ሳንቲም ይሸጥ የነበረው የአንድ ጠርሙስ አረቄ ዋጋ እስከ ሰባት ብር ድረስ ይሸጥ ጀመር፡፡ ቀይ ሽንኩርት በሁሉም ገበሬ ጓሮና በባለርስቱ በገፍ ተዘርቶ ስለነበር፣ እንደ አበሻ አረቄ ዋጋው አልተወደደም፡፡
ስፓኒሽ ፍሉ (የሕዳር በሽታ) መላው አውሮፓን ክፉኛ ባጠቃበት ዘመን በመኖሪያ ቤታቸው መግቢያ በር ላይ ቀይ ሽንኩርት ልጠው ከሰቀሉት ሰዎች ውስጥ አብዛኛዎቹ በበሽታው አልተያዙም ነበር፡፡ ምክንያቱም ቀይ ሽንኩርት በአየር ውስጥ የሚገኙትን ቫይረሶችና ባክቴሪያዎች ወደራሱ ስቦ (ሰብስቦ) በርሱ ላይ በማጣበቅ እንዲሞቱ (እንዲዳከሙ) የማድረግ ወይም እንዳይንቀሳቀሱ (እንዳይራቡ) የማገድ የተፈጥሮ ኃይል ስለአለው ነው፡፡ በሳይንሳዊ ምርምርም ተረጋግጧል፡፡ ተልጦ በቤት ውስጥ በክር የተንጠለጠለ ቀይ ሽንኩርት ጠቁሮ መንምኖ በኖ የሚጠፋው በአየር ውስጥ የሚገኙትን ቫይረሶችና፣ ባክቴሪያዎችን ቀስ በቀስ አጥፍቶ (አድክሞ) በመጥፋቱ ነው፡፡ ቀይ ሽንኩርት በተፈጥሮ ኃይሉ ራሱ እየሞተ የሌላውን ሕይወት ያድናል የተባለለትም ለዚህ ነው፡፡
በሁለተኛ ደረጃም በበሽታው ተይዘው የአበሻ አረቄ ጠጥተው ያልሞቱ ሕመምተኞች (ገመምተኞች) ቶሉ ድነው ከአልጋ ላይ መነሳት ሲያቅታቸው ድካሙ (ድብርቱ) እንዲለቃቸውና ቶሉ እንዲድኑ ተብሎ የደረቀ የበሬ ቆዳ በተኛው በሽተኛ ላይ በድንገት ደብድቦ በማስጮህ በሽተኛው ሲደነግጥ ከበሽታው ሙሉ በሙሉ ድኖ መነሳት ጀመረ፡፡ አይ የአበሻ ጥበብ!!
በሦስተኛ ደረጃም የማበረታቻ ፈዋሽ መድኃኒት የሆነው የደረቀ የበሬ ቆዳ ድብደባው ተሻሽሎ፣ ድብርተኛው በሽተኛ በተኛበት በድንገት በጆሮ ግንዱ ላይ አስጠግቶ፣ ጠመንጃ መተኮስ ዘመናዊና የተቀላጠፈ ፈዋሽ መድኃኒት ሆነ፡፡ በመጨረሻም፣ በሽተኛው በተኛበት በድንገት ጠመንጃ መተኮስ ፈውስ ከሆነ በየቀኑ፣ በየሰዓቱ፣ ጠዋትም፣ ቀንም፣ ማታም ለሊትም ጠመንጃ በየቦታው ከማንጦሻጦሽ ይልቅ በአንድ ቀን፣ በአንድ ለሊት፣ በጋራ በአዲስ አበባ ከተማ ከዳር እስከ ዳር በጠመንጃ ተኩስ በድንገት ከተማዋን ማናወጥ የተሻለ ይሆናል ተብሎ በመንግስት ደረጃ በምስጢር ተመከረበት። እቅዱንም ሕዳር 11 ቀን ምሽት ሌሊቱን ተግባራዊ ለማድረግ ተወሰነ፡፡
ሕዳር 11 ቀን ከጠዋቱ ጀምሮ መንግስት የውጪ ወራሪ ጠላት የመጣ በማስመሰል ሁሉም እንዲጠነቀቅ በነጭ ለባሾቹ በምስጢር እንዲነገር (እንዲወራ) አስደረገና ቀኑን ሙሉ በመንግስት ደረጃ በሹክሹክታ (በድብቅ) ሽብር ሲነዛ ተዋለ፡፡ ቀኑን ሙሉ አዲስ አበባ በወራሪ ጠላት መምጣት ወሬ ስትናወጥ ዋለች፡፡ ገመምተኛ የሆኑ በሽተኞች ይህንን ወሬ ሲሰሙ ተደናግጠው እንደምንም በርትተው ተነስተው ወራሪውን ጠላት ለመዋጋት ተዘጋጁ፡፡ ሕዳር 11 ቀን ምስጢሩን የሚያውቁም የማያውቁም አዛውንትና እስላም ክርስቲያኑ ሁሉ አንድ ላይ ሆነው ተሰባስበው የመጣውን ወራሪ ጠላት ፈጣሪ እንዲመልሰውና ለማሸነፍ ይችሉ ዘንድ ፈጣሪ እንዲረዳቸው ሲፀልዩ ዋሉ፡፡
ምስጢሩን የሚያውቁም የማያውቁም ጐልማሶችም ቀኑን ሙሉ ምሽግ ሲቆፍሩ፤ ጠመንጃቸውን ሲወለውሉ፣ ጦራቸውን ሲሰብቁ፣ ጋሻና ጐራዴአቸውን ሲያጠባብቁ፣ ስንቅ ሲሰንቁ፣ እንደ አንበሳ ሲንጐማለሉና ሲፎክሩ፣ እንደ ነብር ሲንቆራጠጡና ሲያቅራሩ ዋሉ፡፡ ሲመሽም ማታ አንድ ሰዓት ገደማ በምስጢር በታቀደው መሰረት፣ በመንግስት ጀግኖችና ነፍጠኞች (ወታደሮች) የጠመንጃው ተኩስ ከዳር እስከዳር ተጀመረ፡፡ ቀን በወሬ የተፈታችው (የታመሰችው) አዲስ አበባ ማታ በተኩስ ተናወጠች፡፡ ለሊቱን ሙሉ አዲስ አበባ ከተማና ነዋሪዋ በድንገተኛ ተኩስ ሲናጡ አደሩ። ከተኩሱ ብዛት የተነሳ በሰማይ ላይ ጥይት እርስ በርሱ እየተጋጨ እሳት ፈጠረ፡፡ በዚያን ሌሊት በባሩድ ጉም የተሸፈነ የብርሃን ወጋገን ታየ፡፡
በዚህን ጊዜ ዕውነትም ወራሪ ጠላት መጥቶ፣ አዲስ አበባ ገብቷል ተባለና መነሳት ያልቻሉ ገመምተኛ በሽተኞች በሙሉ ተደናግጠው፣ እምቢ ላገሬ እምቢ ለክብሬ ብለው ሊዋጉ ተነሱ፡፡ ታጠቁ፣ ጠመንጃቸውን ተኮሱ፣ ጦራቸውን ሰበቁ፣ ጋሻና ጐራዴአቸውን ይዘው ፎከሩ፣ አቅራሩ፡፡ ሕዳር 11 ቀን ሌሊት ሊነጋጋ ሲል መንግስት ተኩሱን አስቆመ። ነጋ፡፡ ሲነጋ ጠዋት ሕዳር 12 ቀን የባሩድ ጢስ አዲስ አበባ ከተማን ጉም የለበሰች አስመሰላት፡፡ በድብርት የአልጋ ቁራኛ የነበሩት ሕመምተኛ በሽተኞች ሁሉ በተኩሱ ብዛትና ድንጋጤ፣ በባሩዱ ሽታ፣ በብሔራዊ ንዴትና ቁጣ ምክንያት ሙሉ በሙሉ ድነው ተነሱ፡፡ የአበሻ ጥበብ አይገርምም??
በአበሻ አረቄ አከርካሪውን የተመታው ስፓኒሽ ፍሉ (የሕዳር በሽታ) ሙሉ በሙሉ ተደምስሶ ከኢትዮጵያ ሲጠፋ ጨካኝ (ሳዲስት) የዓለም ሳይንቲስቶች ክፉኛ አፈሩ፡፡ ለምን ይሆን?
እነሆ እስከዛሬ ድረስ ሕዳር 12 ቀን በከተማውም ሆነ በገጠሩ ጢስ የሚሰጠው ኋላቀር ባህላዊ ልማድ ሆኖ ሳይሆን፡-
1ኛ. በስፓኒሽ ፍሉ (ሕዳር በሽታ) ወረርሽኝ በሽታ በርካታ ኢትዮጵያውያንና የዓለም ሕዝብ ሰለባ የሆነበት፣ ያልተመዘገበ ብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ የሰማዕታት ቀን በመሆኑ ነው፡፡
2ኛ. የስፓኒሽ ፍሉ (የሕዳር በሽታ) መድኃኒት በኢትዮጵያ ውስጥ ተገኝቶ፣ በሽታው ድል የተደረገበት የድል ቀን በመሆኑ ነው፡፡
ክብር ለኢትዮጵያ!!

Read 10884 times