Saturday, 14 November 2015 09:34

ቢቢሲ በኢትዮጵያ ድርቅ ላይ ያቀረበው ዘገባ አነጋጋሪ ሆኗል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(12 votes)

መንግሥት “ረሃብ አልተከሰተም” ብሏል

   ሰሞኑን ቢቢሲ በሰሜን ኢትዮጵያ ወሎ አካባቢ ተገኝቶ ድርቁ ባስከተለው ረሃብ ላይ ያቀረበው ዶክመንተሪ፤ በተለያዩ አለማቀፍ ሚዲያዎች አነጋጋሪ ሆኖ የሰነበተ ሲሆን መንግስት በድርቁ የሰው ህይወት አልፏል የሚባለውን አልቀበልም ብሏል፡፡
በ1977 ዓ.ም የተከሰተው አስከፊ ድርቅ የብዙዎችን ህይወት በቀጠፈበት ወሎ ቆቦ አካባቢ የቢቢሲው ጋዜጠኛ ክሊቭ ማይሬ ተገኝቶ፣ ልጇን በሞት ያጣች ብርቱካን አሊ የተባለች እናትንና የአካባቢውን ነዋሪዎች አነጋግሮ በሠራው ዘገባ፤ በድርቁ በአንድ አካባቢ ብቻ በየቀኑ ሁለት ህፃናት እየሞቱ መሆኑን ጠቁሟል - የተባበሩት መንግስታት ሪፖርትን በመጥቀስ፡፡
በአካባቢው የተከሰተው ድርቅ ከ30 አመት በፊት ከተከሰተው የ1977 ድርቅ ያልተናነሰ መሆኑን ተጐጂዎቹ እንደነገሩትም ጋዜጠኛው ገልጿል፡፡ ልጇን በረሃቡ የተነሳ በሞት እንዳጣች የገለፀችው ብርቱካን አሊም ሆነች የአካባቢው ነዋሪዎች በቂ ምግብ እያገኘን አይደለም ማለታቸውን ጋዜጠኛው ነግረውኛል በማለት ዘግቧል፡፡
የክረምቱ የበልግ ዝናብ አልነበረም፤ የክረምቱ መግቢያ ላይ ያገኘነውን ትንሽ ዝናብ ተማምነው የዘሩት የማሽላ ቡቃያ፣ ዝናቡ በዚያው በመቅረቱ አይናቸው እያየ ደርቆ መጥፋቱን ነዋሪዎች ተናግረዋል - ለቢቢሲ፡፡በድርቁ የተነሳ ከብቶች የሚመገቡትና የሚጠጡት ውሃ ማጣታቸውንና ችግሩ ወደተባባሰ ሁኔታ እያመራ መሆኑን ያወሳው ጋዜጠኛው፤ አለማቀፉ ማህበረሰብ ለችግሩ አስቸኳይ እርዳታ ማድረግ እንዳለበት አሳስቧል፡፡
በእንግሊዝ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የቢቢሲን ዘገባ ፍፁም የተጋነነ ነው ሲል የተቃወመ ሲሆን በየቀኑ ሁለት ህፃናት ይሞታሉ የተባለውም ከእውነት የራቀ መሆኑን ጠቁሞ፤ ድርቁ ያስከተለው ጉዳት ከ1977 ጋር መመሳሰሉም ተገቢ አለመሆኑን ገልጿል፡፡
ዊሊያም ዴቪሰን የተባሉ ፀሐፊ “ዘ ጋርዲያን” ጋዜጣ ላይ ባቀረቡት ሰፊ ጽሑፍ፤ የቢቢሲ ዘገባ መጠነኛ ግነት አለበት ሲሉ የተቹ ሲሆን የኢትዮጵያ መንግስት አደጋውን ለመቋቋም እያደረገ ያለው ጥረትም በቂ እንዳልሆነና መዘናጋት እየታየበት መሆኑን አመልክተዋል፡፡
“ሁለት ህፃናት እየሞቱ ነው የሚለው ዘገባ መረጃን መሠረት ያደረገ አይደለም፤ ጉዳቱም ከ1977 ጋር የተመሳሰለበት መንገድ ትክክል አይደለም” ብለዋል ፀሐፊው፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግስት ድርቁን በራሱ አቅም ብቻ መቋቋም እንደሚችል አድርጐ ማቅረቡ አለማቀፍ ማህበረሰቡ ችግሩን በአፋጣኝ ተረድቶ ልገሣ እንዳያደርግ የሚያዘናጋ ነው ብሏል፡፡ “መንግስት ምንም እንኳ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ ለውጥ ያመጣ ቢሆንም እስከ 15 ሚሊዮን ህዝብ ይጐዳል የተባለውን የድርቅ አደጋ በራሱ አቅም መወጣት አይችልም” ያለው ፀሐፊው፤ መንግሥት አስቸኳይ እርዳታ ሊጠይቅ እንደሚገባ አሳስቧል፡፡
“ኢትዮጵያ በየ10 ዓመቱ በአስከፊ ድርቅ ትመታለች” በሚል ርእስ ሰፊ ዘገባ ያጠናቀረው አልጀዚራ በበኩሉ፤ ድርቁ በጐዳቸው አካባቢዎች፣ ገበሬዎች ቡቃያቸው ባለበት ደርቆ እየጠፋ፣ አርብቶ አደሮች ከብቶቻቸው እየሞቱባቸው መሆኑን አመልክቷል፡፡
የአልጀዚራ ዘጋቢ በምስራቅ የኢትዮጵያ አካባቢ ተገኝቶ ያነጋገረው ኦማር መሃመድ የተባለ አርሶ አደር፤ “ቡቃያዎቻችን ደርቀዋል፤ እኛም ባዶ እጃችንን ቀርተናል” ብሏል፡፡ ልጆቹን ለመመገብም ከሶስት ላሞቹ አንዷን ሸጦ ምግብ ለመግዛት መገደዱን ኦማር ገልጿል፡፡
“የምንበላው የለንም፣ ምግብና ውሃ እንፈልጋለን” ያለው ኦማር፤ እስካሁን ከለጋሽ ድርጅቶችም ሆነ ከኢትዮጵያ መንግስት ያገኘው እርዳታ እንደሌለ ተናግሯል፡፡ ሌላው አርብቶ አደር መሃመድ ፋኒ በበኩሉ፤ ከነበሩት ከብቶች 40 ያህሉ ሞተው፣ 5ቱ ብቻ መቅረታቸውን ለአልጀዚራ ተናግሯል፡፡ “መጀመሪያ ከብቶቹ ሞቱብኝ፤ አሁን ደግሞ ግመሎቼና ፍየሎች እየሞቱብኝ ነው” ብሏል - መሃመድ፡፡
የግብርና ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ብርሃኑን በጉዳዩ ላይ ማነጋገሩን የጠቆመው አልጀዚራ፤ “መንግሥት የዜጐችን ህይወት ለማዳን ከራሱ በጀት መድቦ እየተንቀሳቀሰ ነው፤ ቀደም ሲል ከብቶች ቢሞቱብንም በአሁኑ ሰዓት መንግሥት መኖ በማቅረብ ላይ ነው” ማለታቸውን ጠቅሷል፡፡
በትናንትናው ዕለት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በድርቁ ዙሪያ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ መንግስት በድርቁ ለተጐዱ አካባቢዎች በየነጥብ ጣቢያው እርዳታ እያቀረበ መሆኑንና የእርዳታ ማከፋፈያ ጣቢያዎችን የሚመራ ብሄራዊ ኮሚቴ መቋቋሙን አስታውቀዋል፡፡
እስካሁን ለተረጂዎች ከተከፋፈለው እርዳታ በተጨማሪም 600 ሺህ ሜትሪክ ቶን እህል ከውጭ ለመግዛት ማዘዙንና ከዚህ ውስጥ 200 ሺህ ሜ.ቶን ያህሉ ጅቡቲ ወደብ መድረሱን፣ በቅርቡም ወደ ሀገር ውስጥ ገብቶ ለተረጂዎች እንደሚደርስ አስታውቀዋል - አቶ ደመቀ፡፡
በተለያዩ የውጭ መገናኛ ብዙሃን፣ በድርቁ የተነሳ የሰው ህይወት አልፏል በሚል የተሰራጨውን ዘገባ አስመልክቶ ምክትል ጠ/ሚኒስትር ደመቀ ሲናገሩ፤ “የውጭ መገናኛ ብዙሃን ከተለያዩ አካላት ጋር እንደሚሰሩ ይታወቃል፤ ከዚያ በላይ ግን አፍ ለማዘጋት አልያም ለማስተባበልና ምላሽ ለመስጠት ሳይሆን ረሃብ የሚባል ነገር ኢትዮጵያ ውስጥ የለም” ብለዋል፡፡
እርዳታ ባለመድረሱ ረሃብ የተከሰተበት ሁኔታ አለመኖሩን፣ ስደትም አለመታየቱን አቶ ደመቀ ጠቁመው፤ “በየትኛውም ጊዜ በማንኛውም መንገድ በህይወት ያለ ሰው ህይወቱ ሊያልፍ ይችላል፤ ዋናው ጥያቄ ህልፈቱ የተከሰተው በረሃብ ነው ወይ የሚለውን ለማየት ህዝቡ ውስጥ ገብቶ ማየት አሳማኝ ይሆናል” ብለዋል፡፡በድርቁ የተጠቁት አካባቢዎች ወትሮም ድርቅ የማያጣቸው የአርብቶ አደሩ አካባቢዎች መሆናቸውን ለሮይተርስ የገለፁት የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አብዱል አዚዝ መሃመድ በበኩላቸው፤ የድርቁ ችግር ሃገሪቱ በያዝነው ዓመት ለማስመዝገብ ባቀደችው የ10 በመቶ አጠቃላይ እድገት ትንበያ ላይ ምንም አሉታዊ ተፅእኖ እንደማይኖረው ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል የድርቁ አደጋ የተራዘመ ሊሆን ይችላል ያለው የተባበሩት መንግሥታት፤ እስከ 600 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ እርዳታ እንደሚያስፈልግም ገልጿል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት እስካሁን 192 ሚሊዮን ዶላር መድቦ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ታውቋል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ሰሞኑን የአሜሪካ መንግስት ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ፣ የቻይና መንግስት ደግሞ 163 ሚሊዮን ብር እርዳታ ለድርቁ ለግሰዋል፡፡
35ኛ አመቱን እያከበረ ያለው የብሔረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) በበኩሉ፤ ትናንት 30 ሚሊዮን ብር መለገሱን አስታውቋል፡፡

Read 13742 times