Saturday, 24 October 2015 09:49

ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ የ330 ሺህ ብር ክስ ቀረበበት

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(24 votes)

“ዴርቶጋዳ” በተሰኘው የመጀመሪያ ረዥም ልብወለዱ ዕውቅና ያተረፈው ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ፤ በአይናለም የመጽሐፍት መደብር ባለቤት፣ በአቶ አይናለም መዋ የ330 ሺህ ብር  ክስ እንደቀረበበት ምንጮች ጠቆሙ፡፡ ከክስ መዝገቡ ላይ ለመረዳት እንደተቻለው፤ ደራሲ ይስማዕከ ወርቁ “ዴርቶጋዳ” እና “ዣንቶዣራ” የተሰኙ መጽሐፎቹን በራሱ ማተሚያ ቤት አሳትሞ ለአይናለም መዋ ለመስጠት ከተዋዋለ በኋላ፣ ውሉን አፍርሶ ከሌላ ሰው ጋር ተዋውሏል፡፡ አይናለም የመፅሀፎቹን ዋጋ አስቀድሞ መክፈሉም በክሱ ተጠቅሷል፡፡ ደራሲው መጽሐፎቹን አትሞ ለመስጠት የተዋዋለው እስከ ሰኔ 4 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ የነበረ ቢሆንም “ዴርቶጋዳ” የተሰኘውን መጽሐፍ 5ሺህ ኮፒ አሳትሞ ለመስጠት ተዋውሎ 2ሺህ ኮፒ ብቻ ለውል ሰጪው በማድረስ ቀሪውን 3ሺህ ኮፒ ለሌላ ሰው ከውል ውጪ ማስተላለፉ በክሱ ላይ ተገልጿል፡፡ ክሱ የቀረበለት ፍ/ቤትም፤ ተከሣሽ ቀርቦ ምላሽ እንዲሰጥ ለፊታችን ሰኞ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ደራሲና አሣታሚ ይስማዕከ ወርቁ በበኩሉ፤ ስለክሱ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ለአዲስ አድማስ በስልክ በሰጠው ምላሽ ገልጿል፡፡ አስራ አንደኛ መፅሀፉን ለማውጣት በማስተዋወቅ ላይ የሚገኘው ዝነኛው ደራሲ ይስማዕከ፤ “ዴርቶጋዳ” የተሰኘ የመጀመሪያ ልብወለዱ ከ200ሺ በላይ ቅጂዎች እንደተሸጡለት ይታወቃል፡፡ የሙሉ ጊዜ ደራሲ የሆነው ይስማዕከ፤ በአዋሳ የህክምና ትምህርቱን አጠናቋል፡፡  

Read 15539 times