Saturday, 10 October 2015 15:56

ሠማያዊ ፓርቲ የተከሰተው “ረሃብ” የፖሊሲ ውድቀት ያመጣው ነው አለ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(10 votes)

ጉዳዩን ለአለም የሚያሳውቅ ገለልተኛ አካል እንዲቋቋም ጠይቋል
                                
    ሠማያዊ ፓርቲ፤ በኢትዮጵያ የተከሰተው “ረሃብ”፤ ከገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት የመነጨ ነው በማለት ችግሩን ለአለም የሚያሳውቅ ገለልተኛ አካል እንዲቋቋምና አለማቀፉ ህብረተሰብ እርዳታውን እንዲለግስ ጠየቀ፡፡ ፓርቲው ከትናንት በስቲያ “ረሃቡ የገዥው ፓርቲ የፖሊሲ ውድቀት ነው!” በሚል ርዕስ በሠጠው መግለጫ፤ ችግሩ ከተፈጠረ በኋላ አለማቀፉ ማህበረሰብ ለዜጐች እርዳታ እንዳያቀርብ መንግስት ጉዳዩን ሲሸፋፍን ቆይቷል ሲል ተችቷል፡፡
“መንግስት የኋላ ኋላ ከአቅሙ በላይ ሲሆንበት ችግሩ እንደተከሰተ ቢገልጽም ዜጐች ተገቢውን እርዳታ በሚያገኙበት መልኩ እርምጃ እየተወሰደ አይደለም” ብሏል ፓርቲው በመግለጫው፡፡ የተከሰተው ችግር የፖሊሲ ውድቀትን ያመላክታል ያለው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ገዥው ፓርቲ ቆሜለታለሁ የሚለውን አርሶ አደርና አርብቶ አደር ህይወት ለማሻሻል የረባ ስራ እንዳልሠራ ማረጋገጫ ነው ብሏል፡፡ “ግብርናው ኢኮኖሚውን ይመራል የሚለው በተግባር አልታየም፤ ምክንያቱም ሚሊዮኖች በየአመቱ ለ“ረሃብ” ችግር መጋለጣቸውን ቀጥለዋል” ሲል ገልጿል ፓርቲው፡፡
ለተከሰተው ሀገራዊ ችግር መንግስት አፋጣኝ እርምጃዎችን እንዲወስድ ያሳሰበው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ስለ ችግሩ ለኢትዮጵያውያንና ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ የሚያስረዳ ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ፤ በችግሩ ለተጠቁ ዜጐች መፍትሔ እንዲፈለግ ጠይቋል፡፡
የምግብ እጥረቱ (ረሃቡ) ከተፈጠረባቸው አካባቢዎች መረጃ በማሰባሰብና በማጣራት ለህዝብ በየጊዜው እንደሚያሳውቅ የገለፀው ፓርቲው፤ በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ኢትዮጵያውያንና የአለም ህብረተሰብ ከተጐጂዎች ጐን እንዲቆሙ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
መንግስት በበኩሉ፤ ችግሩ የተፈጠረው በአለማቀፍ ደረጃ ከተከሰተው የአየር ፀባይ ለውጥ (ኤሊኖ) ጋር ተያይዞ መሆኑን በመግለፅ፣ በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ዝናብ ባለመዝነቡ የምግብ እጥረት ቢያጋጥምም “ረሃብ” አለመከሰቱን በተደጋጋሚ አስታውቋል፡፡

Read 2501 times