Saturday, 03 October 2015 09:52

ከፓርላማው ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠቅም ነገር ይገኛል ብለን አናምንም ተቃዋሚዎች

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(13 votes)

“መንግሥት ተቃዋሚዎችን አወያያለሁ
የሚለው ለፖለቲካ ፍጆታ ብቻ ነው”

አንድም ተቃዋሚ ፓርቲ ወይም የግል ተወካይ የማይኖርበት 5ኛው የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የፊታችን ሰኞ የሚመሰረት ሲሆን ም/ቤቱ አማራጭ የፖሊሲ ሃሳቦችና የሰሉ ትችቶች የማይደመጡበት እንደሚሆን ተቃዋሚዎች ገለፁ፡፡
በፓርላማው የተቃዋሚ ፓርቲ ድምፅ አለመኖር ህዝቡን ይጐዳል ያሉት የመድረክ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ፤ “ከዚህ ቀደም በፓርላማ በነበረን ጊዜ ያለመታከት የህዝብን ሰቆቃና እሮሮ ስናሰማ ነበር፤ አሁን ፓርላማው ከዚህ አይነቱ ጥያቄና አስተያየት ውጭ ነው” ብለዋል፡፡  በውጭም በሃገር ውስጥም ከማንኛውም መድረክ ይልቅ ተደማጭ የሚሆነው በፓርላማ የሚሰነዘር ሃሳብ ነው የሚሉት ፕ/ር በየነ፤ ይህ መድረክ አለመኖሩ ተቃዋሚው በሃገሩ ጉዳይ ያለውን ሃሳብ ህብረተሰቡ እንዳይረዳ እንቅፋት ይሆናል ብለዋል፡፡
ገዢው ፓርቲ እንደ ተምሳሌት ከሚከተለው የቻይና መንግሥት ጋር በዚህ ረገድ በሚገባ ተቀራርበዋል ያሉት ፕ/ሩ፤ ይህ ሁኔታ ግን ለኢትዮጵያ ህዝብ አደገኛ እንደሆነና የህዝብ እውነተኛ ድምፅ ሊታፈን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያውያን ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ኢዴፓ) ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፤ “እስከዛሬ ከመንግሥት ጋር ተቀራርበን ለመስራት ያደረግነው ጥረት ውጤት አላስገኘም፣ ከዚህ በኋላ ትኩረት ሰጥተን የምንሰራው የስርዓት ለውጥ እንዴት መምጣት አለበት በሚለው ላይ ነው” ብለዋል፡፡  
የመድብለ ፓርቲ ስርአት ፍፁም የደበዘዘበትና ህዝቡ ተስፋ የቆረጠበት ሁኔታ ነው የሚታየው የሚሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ፓርላማውም ቢሆን የአንድን ፓርቲ አስተሳሰብ በቻ የሚያንፀባርቅ በመሆኑ ለመጪዎቹ 5 አመታት ከፓርላማው ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠቅም ነገር ይገኛል ብለን አናምንም ብለዋል፡፡
በፓርላማው የህግና የፖሊሲ ክርክር አድርጐ ለውጥ ለማምጣት ገዢው ፓርቲ ፍላጐት የለውም የሚሉት ዶ/ር ጫኔ፤ ምናልባት ይህ አካሄድ የተቃዋሚ ሃሳቦችን ከመድረኩ የማጥፋት ስትራቴጂ ውጤት ሊሆን ይችላል ይላሉ፡፡
የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሃሪ ደግሞ አዲስ የሚመሰረተው ፓርላማ  ለሃገሪቱም ሆነ ለመንግስት አይበጅም ባይ ናቸው፡፡  ምክንያታቸውን ሲጠቅሱም፤ ፓርላማው ሁሉን አቀፍ አሳታፊ ባለመሆኑ ነው ይላሉ፡፡ “አሳታፊ ያልሆነ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ደግሞ በምንም መልኩ ውጤታማ ይሆናል የሚል እምነት የለኝም” ብለዋል አቶ አበባው፡፡
የተቃዋሚዎች ድምፅ በፓርላማ አለመኖሩ እምብዛም እንደማያሳስበው የሚገልፀው መንግሥት በበኩሉ፣ በሌላ መንገድ ከተቃዋሚዎች ጋር የተለያዩ የውይይት መድረኮችን በመክፈት በሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ውይይት አደርጋለሁ ብሏል፡፡ በኢህአዴግ 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ መንግስታቸው ከተቃዋሚዎች ጋር በወሳኝ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ዝግጁ እንደሆነ  ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡
ተቃዋሚዎች ግን በጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር እምነት እንደሌላቸው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
መድረክ በተደጋጋሚ ከገዢው ፓርቲ ጋር ለመወያየት ያቀረባቸው ጥያቄዎች ምላሽ አለማግኘታቸውን የሚያስታውሱት ፕ/ር በየነ፤ “የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም እንደ ወቅቱ  ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሁሉ ተቃዋሚዎችን እናወያያለን ሲሉ የነበረ ቢሆንም አንድም ቀን አላወያዩንም፤ አሁንም እናወያያለን የሚለው ሃሳብ የለጋሾችን ቀልብ ለመግዛት ካልሆነ በስተቀር ተግባራዊ የሚሆን አይደለም ብለዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ መድረክ አሁንም ከመንግሥት ጋር ለመወያየት ጥረት እንደሚያደርግ ፕሮፌሰር በየነ ገልፀዋል፡፡ ፡
የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፤ በየጊዜው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተቃዋሚዎችን እናወያያለን የሚሉት  ፈፅሞ አምባገነናዊ ስርአት ነው ላለመባልና ዲሞክራሲያዊ ስርአት ያለ ለማስመሰል ነው ብለዋል፡፡ “አንድም ቀን መንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲን  አቅርቦ አወያይቶ አያውቅም፣ በየጊዜው እናወያያለን ቢልም ወደ ተግባር ሲቀየር አላየንም” ብለዋል ዶ/ር ጫኔ፡፡ ነገሩ ከፖለቲካና ዲፕሎማሲያዊ ንግግር የዘለለ አይደለም ባይ ናቸው፡፡
የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መሃሪም የሁለቱን ፖለቲከኞች ሃሳብ ይጋራሉ፡፡  መንግሥት በተደጋጋሚ ተቃዋሚዎችን አወያያለሁ ቢልም እስከዛሬ ሲፈጽመው አልታየም፤ ለወደፊትም ያነጋግረናል የሚል ተስፋ የለኝም ይላሉ፡፡ “በትክክል ዲሞክራሲን ለማስፈን የሚደረግ ጥረት ያለ አይመስለኝም፤ ተቃዋሚዎች ‘አባሎቻችን ላይ ወከባና ድብደባ ደረሰብን’ ሲሉ ጆሮ ዳቦ ልበስ እየተባሉ፣ መንግሥት በምን ጉዳይ አወያያለሁ እንደሚል አይገባኝም” ብለዋል፡፡
የህዝብ ውይይት እየተካሄደበት እንደሆነ በሚነገርለት 2ኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዙሪያ መንግሥት ተቃዋሚዎችን እንደሚያወያይ መግለፁ የሚታወቅ ሲሆን በቅርቡም ለሁሉም ፓርቲዎች በስልክ የውይይት ግብዣ ጥሪ መደረጉንና ተቃዋሚዎችም ጉዳዩ በደብዳቤ  ተጠቅሶ ጥሪ ይቅረብልን የሚል ምላሽ መስጠታቸው ታውቋል፡፡ ይህን ተከትሎም በደብዳቤ ጥሪ ይደረግላችኋል እንደተባሉና የውይይት ጊዜው እንደተቀየረም ተቃዋሚዎቹ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

Read 3063 times